ቀጥታ፡

በዞኑ በማር ምርት የተገኘው ውጤት ተጠናክሮ ይቀጥላል

ዲላ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በማር ምርት የተገኘውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያስችሉ ተግባራትን መጀመራቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ።

የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዞኑ እየተከናወነ ያለውን የጥምር የግብርና ስርዓት ለንብ ማነብ ስራ አመቺ ሁኔታ በመፍጠሩ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን ተችሏል።

በጥምር ግብርናው ቡና፣ ፍራፍሬ፣ ሃገር በቀል ዛፎችንና የተለያዩ እጽዋቶችን ከማልማት ባለፈ ለንብ ማነብ ስራዎችም የተመቸ ምህዳር ፈጥሯል ነው የሚሉት።

በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በዞኑ ከተከናወነው የንብ ሃብት ልማት ስራ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱ ተገልጿል።

በዚሁ ወቅት በተለይ ተራሮችን የማር ምርት ማዕከል ለማድረግ በተደረገው ጥረት በዲላ ዙሪያ፣ ወናጎ፣ ይርጋጨፌና ኮቾሬ ወረዳዎች በተመረጡ ቦታዎች ከአንድ ሺህ በላይ ዘመናዊ ቀፎ ማስቀመጥ መቻሉን ተናግረዋል።

በንብ ማነብ ስራ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች በተጨማሪ በማህበር የተደራጁ ወጣችን ወደ ስራው እንዲገቡ ማድረግ በመቻሉ በዘርፉ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን እንደተቻለም ነው የገለጹት።

በአዲሱ በጀት ዓመትም የአካባቢውን የደንና የእጽዋት ሽፋን በመንከባከብ ንብ በማነብ ከማር ምርት የሚገኝ ገቢን ከፍ ለማድረግ ወደ ስራ መገባቱን ነው ያመለከቱት።

በወረዳው በራኮ ቀበሌ በግኖ ተራራ ላይ ከ200 በላይ ዘመናዊ ቀፎዎች በማስቀመጥ የንብ ማነብ ስራ እየተካሄደ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የኮቾሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ዳዊቶ ጀቦ (ዶ/ር) ናቸው።

ይህም የማር ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፍ የተፈጥሮ ጸጋዎችን በመንከባከብና በማልማት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በተጨማሪም ጥራት ያለው የተፈጥሮ ማር በማምረት ለአካባቢው አርሶ አደሮች፣ ወጣቶች እና ሴቶች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ መፍጠር እንደተቻለም ነው ያነሱት።

በማር ምርት ስራ ላይ የተሰማሩት አርሶ አደር ብዙነሽ ሐልቹ፤ ከ70 በላይ በሆኑ ባህላዊና ዘመናዊ ቀፎዎቻቸው በአመት ሁለት ጊዜ የማር ምርት እንደሚያገኙ ነው የተናገሩት።

የማር ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆኑንም ነው የተናገሩት።

ከዘመናዊ ቀፎ የሚገኝ የማር ምርት የተሻለ ጥራትና ብዛት ያለው መሆኑን ያነሳው ደግሞ በማር ምርት ስራ ላይ የተሰማራው ወጣት ማርቆስ ጌታሁን ነው።

በወረዳው ያለው የተፈጥሮ ሃብት ለንብ ማነብ ስራ ምቹ በመሆኑም ጥራት ያለው ማር በማምረት በስፋት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆኑን ነው የተናገረው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም