የዲጂታላይዜሽን ጉዞው በከተማው የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን የሚያሳልጥ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የዲጂታላይዜሽን ጉዞው በከተማው የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን የሚያሳልጥ ነው
ወልድያ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የዲጂታላይዜሽን ጉዞው በከተማው የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን እያሳለጠ መሆኑን የወልድያ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ገለጹ።
በወልድያ ከተማ የ‘ነገ’ ቀንን ምክንያት በማድረግ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።
የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ አቶ ንጉስ ዝናቡ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ እየተተገበረ የሚገኘው የዲጂታላይዜሽን አሰራር የከተማዋን እድገትና የህዝቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል።
በከተማው እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች ተስፋ ሰጪና ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውንም ገልጸዋል።
በተለይም የኮሪደር ልማት፣ የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትና ሌሎች የዲጂታላይዜሽን አሰራሮችን በማስፈን የህዝቡን እርካታ ማሳደግ መቻሉን አስረድተዋል።
በመሆኑም በአዲሱ ዓመት አመራሩና ባለሙያው የቴክኖሎጂ አሰራርን ፈጥኖ በመላመድ፣ እውቀትና ክህሎትን በመጨበጥ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት ራሱን ማዘጋጀት እንዳለበት አሳስበዋል።
የዲጂታላይዜሽን ንቅናቄው የወደፊቷን የወልድያ እድገት በፅኑ መሰረት ላይ ለመገንባትና የህዝቡን እርካታ ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑንም አስገንዝበዋል።
የከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ኢትዮጵስ አያሌው ፤ በከተማዋ የተጀመሩት የስማርት ሲቲና የዲጂታል አሰራሮች በህብረተሰቡ ዘንድ የሚነሱ የመልካም አስተዳደርና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን እየፈቱ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የመሬት፣ የንግድ፣ የኮንስትራክሽንና የከተማ ፕላን መረጃዎችን ወደ ዲጂታል ሲስተም በማስገባት ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሰራርን ለማስፈን የተደረገው ጥረት አበረታች መሆኑንም አፈ ጉባኤው ተናግረዋል።
የከተማ አስተዳደሩን አሰራሮች ወደ ዲጂታል ስርዓት የመቀየር ስራ ተጨባጭ ውጤት እያመጣ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ጽህፈት ቤት የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ቡድን መሪ አቶ ብርሃኑ እንዳውቄ ናቸው።
ለዚህም በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከ11 በላይ ሲስተሞችን በመዘርጋት ከ82 በላይ የአገልግሎት አይነቶችን ለተገልጋዩ ማህበረሰብ መስጠት መቻሉን ገልጸዋል።
በዚህም ከሁለት ሺህ በላይ ለሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ፈጣን፣ ፍትሃዊና ከብልሹ አሰራር የጸዳ አገልግሎት መስጠት መቻሉን አስረድተዋል።
በተጨማሪም በከተማዋ የሲሲቲቪ (CCTV) ካሜራ፣ የስማርት ስክሪንና የስማርት ትራንስፖርት ትግበራ መጀመሩን ነው የተናገሩት።
በወልድያ ከተማ በተካሄደው የፓናል ውይይት ላይ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ ባለሙያዎችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊ ሆነዋል።