ቀጥታ፡

የመሶብ አንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት የዜጎችን የአገልግሎት እርካታ ያሳደገ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ያስቻለ ነው

አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የመሶብ አንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት የዜጎችን የአገልግሎት እርካታ ያሳደገ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ያስቻለ መሆኑን የአዲስ አበባ ፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ቢሮ ገለጸ። 

የአገልግሎቱን ተደራሽነት ይበልጥ ለማስፋፋት እየተሠራ መሆኑም ተጠቁሟል።


 

የጳጉሜን 5 "የነገ ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት የተዘጋጀና የማዕከሉን የአንድ ዓመት ጉዞ የሚያስቀኝ የፓናል ውይይት "ከአገልግሎት ስብራት ወደ ዲጂታል ብስራት" በሚል መሪ ሐሳብ እየተካሄደ ይገኛል።

በውይይቱ ላይ የአዲስ አበባ ፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ቢሮ በቢሮ ኃላፊ ደረጃ የአገልግሎት አሰጣጥና አውትሶርስ ዘርፍ ኃላፊ አቶ በቀለ ተመስገን እንደተናገሩት፤ ከዚህ ቀደም የነበረው የአገልግሎት አሰጣጥ ዜጎችን ለእንግልት የሚዳርግና የግልጽነት ችግር የነበረበት ነው፡፡

ከ100 ዓመታት በላይ የተሻገረው የሀገራችን የሲቪል ሰርቪስ ሥርዓት የዜጎችን ፍላጎት ማሟላት በማያስችል የተወሳሰበ ቢሮክራሲ የተሳሰረና የአገልግሎት ስብራት የነበረበት በመሆኑ ለልማት ማነቆ ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል።

መንግሥት በዘርፉ ያካሄደው ሪፎርም በዘርፉ የነበሩ እንቅፋቶችን ከመሠረቱ የፈታ፣ የዲጂታል አገልግሎት አሰጣጥ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን የፈታ፣ የዜጎችን እርካታ ያሳደገ፣ እንዲሁም አሠራሩን ፈጣን፣ ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተጠያቂነት የሰፈነበት ያደረገ መሆኑን አስረድተዋል።

ዲጂታል ቴክኖሎጂ የህልውናና የዘመናዊነት መገለጫ መሆኑን የጠቆሙት ኃላፊው፤ የመሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት እስካሁን ለ700 ሺህ ያህል ዜጎች አገልግሎት መስጠት መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት ዓለም አቀፍ መስፈርቶችን ያሟሉ 11 ማዕከላትና 1 ተንቀሳቃሽ የማዕከል አገልግሎት ለህብረተሰቡ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመው፤ በቀጣይም 3 ተጨማሪ ተንቀሳቃሽ አገልግሎት መስጫዎችና 20 ተጨማሪ የመሶብ ማዕከላት ተገንብተው ወደ ሥራ እንደሚገቡ አስታውቀዋል።

 

 

 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም