ቀጥታ፡

የዲጂታል የመሬት መረጃ ሥርዓት የከተሞችን የመሬት አስተዳደር ያዘምናል

አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):- ሁለገብ የመሬት መረጃ ሥርዓት የከተሞችን የመሬት አስተዳደር ወደ ዲጂታል ሥርዓት በማሸጋገር ዘመናዊ፣ ዘላቂ፣ ቀልጣፋ እና ግልጽ የመሬት አገልግሎት ለመስጠት እንደሚያግዝ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ገለጸ።

የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የመሬት አስተዳደር ሥርዓቱን ተግባራዊ ለማድረግና በዘርፉ በጋራ መሥራት በሚያስችላቸው ጉዳዮች ዙሪያ የትብብር ስምምነት በመፈራረም የጋራ መግለጫ ሰጥተዋል።

በከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር የመሬትና ካዳስተር መሪ ሥራ አስፈጻሚ ብዙአለም አድማሱ እንደገለፁት፤ የተቋማቱ ትብብር የኢትዮጵያን የከተማ መሬት መረጃ ሥርዓት ለማዘመንና የመሬት አገልግሎቶችን ይበልጥ ቀልጣፋና ግልጽ ለማድረግ ያለመ ነው።

ሥርዓቱ ሀገሪቱ ከሕጋዊ ካዳስተርና ከፊስካል ካዳስተር ወደ የተቀናጀ ሁለገብ ካዳስተር ሥርዓት የምታደርገውን ሽግግር የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል።

የሕጋዊ ካዳስተር ሥርዓት የዜጎች፣ የመንግሥትና የባለሀብቶችን የመሬት ይዞታና ሕጋዊ ሰነዶች በግልጽ እንዲመዘገቡ በማድረግ የይዞታ ዋስትናንና የንብረት መብትን እንደሚያጠናክርም አመልክተዋል።

የፊስካል ካዳስተር ደግሞ የመሬትና የንብረት ግምት መረጃዎችን ከካዳስተር ካርታ ጋር በማገናኘት ፍትሃዊና ትክክለኛ የንብረት ግብር ሥርዓት መዘርጋት ያስችላል ነው ያሉት።

የትብብር ስምምነቱ የብሔራዊ የተቀናጀ የመሬት መረጃ ሥርዓትን ማልማትና ማዘመን፣ የንብረት ግብር ሥርዓትን ማሻሻልና በከተሞች በስፋት ተግባራዊ ማድረግን የሚያካትት መሆኑን ገልጸዋል።

በፌዴራል፣ በክልልና በከተማ ተቋማት መካከል የመሬት መረጃ ልውውጥን ማቀላጠፍ፣ የመረጃ አስተዳደርና ተናባቢነትን ማጠናከር እንዲሁም የኢ-ላንድ አገልግሎትና ዲጂታል የሥራ ሂደቶችን ማስፋት የስምምነቱ አካል መሆናቸውን አስታውቀዋል።

ሁለቱ ተቋማት የመሬትና የካዳስተር ሥርዓቶች፣ የንብረት ምዝገባና የንብረት ግብር ሥርዓቶች፣ የመረጃ ማዕከላትና የአይሲቲ መሠረተ ልማቶች ከሳይበር ጥቃት እንዲጠበቁም በመረጃ ደህንነት ዘርፍ በጋራ እንደሚሠሩ ገልጸዋል።

የተቋማቱ ትብብር የመሬት አስተዳደርን በቴክኖሎጂ ለማዘመን፣ የመረጃ ደህንነትን ለማጠናከርና ለዜጎች የተሻለ የመሬት አገልግሎት ለማቅረብ የሚያግዝ ሲሆን፣ ከዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ጋርም የሚጣጣም መሆኑን ገልጸዋል።

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጂኦስፔሻልና ስማርት ፔይመንት ማዕከል ዳይሬክተር ቢንያም አበባው በበኩላቸው፣ የመሬት መረጃ ወሳኝ የመረጃ ሀብት በመሆኑ ከሳይበር ጥቃት ለመጠበቅ በጋራ መሥራቱ ትልቅ ጠቀሜታ አለው ብለዋል።

አስተዳደሩ ባለፉት ዓመታት የመሬት ዲጂታላይዜሽንን የሚያግዙ ቴክኖሎጂዎችንና ፕሮጀክቶችን የማልማት ስራዎችን መሥራቱንና የዛሬው ስምምነት የተገኙ ልምዶችን በማሳደግ የሁለገብ ካዳስተር ሥርዓቱን ለተለያዩ ከተሞች ለማስፋት አቅም እንደሚፈጥር አስረድተዋል።

በስምምነቱ የሀገራዊ የተቀናጀ የመሬት መረጃ ሥርዓት ልማትን ማዘመን፣ የንብረት ግብር ሥርዓት፣ የመረጃ አስተዳደር፣ የኢ-ላንድ አገልግሎት፣ የሳይበር ደህንነትና መሠረተ ልማት፣ ዘመናዊ ጂኦስፓሻል ቴክኖሎጂና የ3ዲ ካርታ ሥራዎች ላይ በጋራ እንደሚሰራ ገልፀዋል።

ይህም የመሬት አስተዳደርን በዲጂታል ሥርዓት ለማዘመን ከሚደረገው ጥረት በተጨማሪ የመሬት መረጃ ደህንነትን በማጠናከር ቀልጣፋና አስተማማኝ የመሬት አገልግሎት ለመፍጠር እንደሚያግዝ ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም