አዲሱ ዓመት ሀገራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በላቀ የስራ መንፈስ የተጀመሩ ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚጎለብቱበት ነው - ኢዜአ አማርኛ
አዲሱ ዓመት ሀገራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በላቀ የስራ መንፈስ የተጀመሩ ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚጎለብቱበት ነው
ሐረር ፤ዻጉሜ 5/2018 (ኢዜአ) ፡-አዲሱ ዓመት ሀገራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በላቀ የስራ መንፈስ የተጀመሩ ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚጎለብቱበት ነው ሲሉ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ተናገሩ፡፡
ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በክልሉ “የነገ ቀን” በተከበረበት ዕለት አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ ባስተላለፉት መልዕክት የ2018 ልዩና ታሪካዊ ዓመት ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ለዚህም 7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊና ነፃ በሆነ መልኩ አካሂደን ህዝቡ የሥልጣን ባለቤትነቱን በድምፁ ያረጋገጠበት ታላቅ የዲሞክራሲ መድረክ ያካሄድንበት ነው ብለዋል።
ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር በፍቅርና በጋራ የተሠራበት ማህበራዊ መሰረት በመጣሉ ሀገራዊ መግባባታችን መጎልበቱን ተናግረዋል፤
ለዘመናት የቆዩ መሠረታዊ ልዩነቶቻችንን በውይይትና በሰለጠነ መንገድ ለመፍታት፣ ብሔራዊ መግባባትን ለመገንባትና ለዘላቂ ሰላም መሠረት ለመጣል የተቻለበት ነው ብለዋል።
ከፖለቲካና ዲሞክራሲያዊው ሂደት ጎን ለጎን፣ የዜጎቻችንን ህይወት የሚያሻሽሉ ታላላቅ የማህበራዊና የኢኮኖሚ ልማት ስራዎች በስፋት የተከናወኑበት ዓመትም ነው ሲሉ ገልጸዋል።
ገፅታ የሚቀይሩ የኮሪደር ልማቶች፣ የቱሪዝም መስህቦችና ሰው-ተኮር ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁበት እንደነበረም አንስተዋል።
የግብርናና የአካባቢ ልማት ስራ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ሀገራዊ የምግብ ዋስትናችንን እያረጋገጥን እንገኛለን ሲሉም ነው የተናገሩት።
ዓመቱ ከፍተኛ መነሳሳትና ቁርጠኝነት የታየበት፣ የመላው ህዝባችን ንቁ ተሳትፎና ተጠቃሚነት የተረጋገጠበት መሆኑንም አንስተዋል።
ቀጣዩ 2019 ዓ.ም ሀገራዊ አንድነታችንን የምናጠናክርበት፣ የሕግ የበላይነትን የምናረጋግጥበትና ጠንካራ የልማት መሠረት የምንጥልበት ዓመት ነው ብለዋል።
የከተማና የገጠሩ ነዋሪ ህዝቦች ሁለንተናዊ እና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ልዩ ትኩረት ይሰጣቸዋል ሲሉ አስገንዝበዋል።
በዚህም የከተማ እና የገጠር የኮሪደር እና የመሰረተ ልማት ስራዎች፣ የቅርስ እና የቱሪዝም መስህቦች ጥበቃ፣ የውበት እና ጽዳት ስራዎች፣ የመልሶ ማልማት፣ የግብርና ማዘመንና ምርታማነትን ማሳደግን ጨምሮ የቴክኖሎጂ ተጠቃሚነትን የማሳደግ ተግባራት ተጠናክረው የሚቀጥሉ ይሆናል ነው ያሉተ።
የክልሉን ሰላምና የህግ የበላይነት ይበልጥ በማጠናከር የህዝቡን የመቻቻልና የአብሮነት እሴት የማጠናከር ስራም ትኩረት የሚሰጠው እንደሚሆን ነው ያብራሩት።
በክልሉ ህዝቦች መካከል ለዘመናት ስር የሰደዱት የአብሮነት፣ የመከባበር፣ የወንድማማችነትና የእህትማማችነት አኩሪ እሴቶች በፀና አለት ላይ መትከልም የመደበኛ እቅዶች አካል እንደሚሆን ነው ያመለከቱት።
የኑሮ ውድነት ጫናን የማቃለል፣ የስራ እድል ተጠቃሚነትን የማጎልበት፣ የግል ዘርፉ በኢንዱስትሪና አገልግሎትመስኮች ያለው ተሳትፎ እንዲጠናከር ይደረጋል ብለዋል።
ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ከመሰረታቸው ለመንቀል ግልፅና ተጠያቂነት ያለው የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት መዘርጋትና የስራ ውጤታማነትን ማረጋገጥ ሌላው የአዲሱ ዓመት ቁልፍ ተግባራችን ነው ሲሉም ገልጸዋል።
በመጨረሻም አዲሱ ዓመት የፍቅር፣ የመቀራረብ፣ የመተማመን፣ የአንድነት፣ የትጋት እና የብልፅግና ዓመት እንዲሆን ተመኝተዋል።