ብሔራዊ የፋይዳ መታወቂያ ከኢትዮጵያ ባሻገር በዛምቢያ፣ሞዛምቢክና ቡሩንዲ የሙከራ ትግበራ ሊጀምር ነው - ኢዜአ አማርኛ
ብሔራዊ የፋይዳ መታወቂያ ከኢትዮጵያ ባሻገር በዛምቢያ፣ሞዛምቢክና ቡሩንዲ የሙከራ ትግበራ ሊጀምር ነው
አዲስአበባ፤ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ ብሔራዊ የፋይዳ መታወቂያ ከኢትዮጵያ ባሻገር በዛምቢያ፣ ሞዛምቢክ እና ቡሩንዲ የሙከራ ትግበራ ሊጀምር መሆኑን የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም (ፋይዳ ቨርስ) ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ዮዳሄ አርአያሥላሴ ገለጹ።
በኢትዮጵያ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተመዝጋቢዎች ቁጥር 50 ሚሊዮን መድረሱንም ተናግረዋል።
ዋና ሥራ አስፈጻሚው የነገ ቀንን አስመልክቶ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፥የፋይዳ መታወቂያ “አንድ ሰው አንድ ነው”በሚል መርህ የዲጂታል ማንነትን የመመዝገብና የማረጋገጥ ሥራን እያከናወነ ነው ብለዋል።
ይህም ወንጀልን ለመከላከል፣አገልግሎቶችን በዲጂታል በማስተሳሰር ለማሳለጥና በግለሰቦች፣ በተቋማትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት መካከል አስተማማኝ ትስስርን ለመፍጠር የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።
ፋይዳን ከአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጋር የማሰናሰል ሥራ ተሠርቶ እስካሁን 150 የመንግሥት፣ የግል፣ የስታርታፕ እና ሌሎች ተቋማት በፋይዳ ትስስር ማድረጋቸውን ተናግረዋል።
በፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ከ200 ሚሊዮን በላይ ማንነትን የማረጋገጥ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ የምዝገባ ማዕከላትን የማስፋፋት ሥራ ተሠርቶ የጣቢያዎቹ ቁጥር ወደ 12 ሺህ ገደማ መድረሳቸውን የጠቀሱት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፥ በዚህም እስካሁን 50 ሚሊዮን ሰዎች መመዝገባቸውን አንስተዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም ወደ ሰፊ የዲጂታል መሠረተ ልማት ማዕከል በማደጉ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ሥር በልማት ድርጅትነት መቋቋሙን አስታውሰዋል።
ፋይዳ ቨርስ ከፋይዳ መታወቂያ በተጨማሪ የፋይዳ ዲጂታል ቦርሳ፣ የዲጂታል አገልግሎቶች የንግድና ተቋማት መፍትሔዎችን በተሳለጠ መንገድ ለመስጠት እንደሚሠራ ጠቁመዋል።
ብሔራዊ የፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት በዲጂታል ቴክኖሎጂ እና በማክሮ ኢኮኖሚው ዘርፍ ኢትዮጵያ እያመጣች ያለው አዎንታዊ ለውጥ በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ከፍተኛ ትኩረት ማግኘቱንም ነው ያስረዱት።
ይህም በርካታ የአፍሪካ ሀገራት የኢትዮጵያን ተሞክሮዎች እንዲቀስሙና በትብብር ለመሥራት ከፍላጎት ያለፈ እንቅስቃሴ ውስጥ እንዲገቡ ማድረጉን ገልጸዋል።
በተለይም በዲጂታሉ ዘርፍ በአቅም ግንባታ፣ በማማከርና ዲጂታል ሥርዓት በመገንባት በርካታ ሀገራት ድጋፍ ለማግኘት ፍላጎት አሳይተዋል ነው ያሉት።
ፍላጎት ካሳዩ ሀገራት መካከል የተወሰኑት የመግባቢያ ስምምነቶችን ተፈራርመው ወደ የሙከራ ፕሮጀክት ትግበራ ለመሸጋገር የተዘጋጁ ሀገራት እንዳሉ ጠቁመዋል።
በዚህም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ቴክኖሎጂን በሙከራ ደረጃ በዛምቢያ፣ ሞዛምቢክ እና ቡሩንዲ ተግባራዊ ለማድረግ እንቅስቃሴ መጀመሩን ተናግረዋል።
ይህ እንቅስቃሴ ተቋሙ አፍሪካውያን በራሳቸው አቅምና እርስ በርስ በመደጋገፍ የዲጂታል ሽግግርን ማሳካት እንደሚችሉ የሚያሳይና የደቡብ ለደቡብ ትብብርን ለማጠናከር ትልቅ ሚና የሚጫወት ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያም በአህጉራዊ ኢኒሼቲቮች ትግበራ አርዓያነት ያለው ሚናዋን እንድታጠናክር የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።