የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአንድነትና የጽናት ተሞክሮ ለቀጣይ ትላልቅ ፕሮጀክቶች መሠረት ይሆናል - ኢዜአ አማርኛ
የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአንድነትና የጽናት ተሞክሮ ለቀጣይ ትላልቅ ፕሮጀክቶች መሠረት ይሆናል
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፡-የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን እውን ያደረገው የኢትዮጵያውያን የጋራ ጥረትና ጽናት ተሞክሮ በቀጣይ ለሚከናወኑ ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶች መሰረት እንደሚሆን የፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) ገለጹ።
ዋና ስራ አስፈጻሚው አረጋዊ በርሔ(ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ስኬት ከአንድ ተቋም ወይም ከአንድ ቡድን ጥረት የመነጨ ሳይሆን የኢትዮጵያውያን የጋራ ተሳትፎና ትብብር ውጤት ነው።
ኢትዮጵያ በርካታ ድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ያሏት በመሆኑ የውሃ ሀብቷን በአግባቡ በመጠቀም ተጨማሪ የውሃና የኃይል ልማት ፕሮጀክቶችን ማልማት እንደምትችልም ገልጸዋል።
የውሃ ሀብትን ለኃይል ማመንጫነት በማዋል የሀገር ውስጥ የኃይል ፍላጎትን ከማሟላት ባሻገር ለቀጣናው ሀገራት ኤሌክትሪክ ሀይል በማቅረብ የውጭ ምንዛሬ ማስገኘት የሚያስችል እምቅ አቅም አለ ነው ያሉት።
ይህን እምቅ አቅም ወደ ተጨባጭ ልማት ለመቀየር ዋነኛው መሠረት የሕዝብ ትብብርና ተሳትፎ መሆኑን ጠቁመው፤ በዚህም ትልቅ ሀገራዊ ዓላማዎችን ማሳካት እንደሚቻል የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ተሞክሮ ትልቅ ማሳያ መሆኑን አመልክተዋል።
ዋናው ቁልፉ ነገር መተባበር እንደሆነ አመልክተው፣ በልማት ላይ ትኩረት ከተደረገ ኢትዮጵያን ትልቅ የልማትና የሥልጣኔ ደረጃ ላይ ማድረስ እንደሚቻልም ገልጸዋል።
የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታን እውን ለማድረግ የታየው የህዝብ ጽናት ታሪካዊ መሆኑን ጠቁመው፤ የተገኘው ተሞክሮ ኢትዮጵያ በራሷ አቅም ትላልቅ ፕሮጀክቶችን ማሳካት እንደምትችል ያረጋገጠ ነው ብለዋል።
የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሂደት ኢትዮጵያውያን በአንድነት እና በጽናት ሲቆሙ ትልቅ ሀገራዊ ዓላማን ማሳካት እንደሚችሉ ያሳየ እንደሆነ አመልክተው፤ ይህ የትብብር እና የጽናት መንፈስ በቀጣይ በሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ላይም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስረድተዋል።