ከሀገራዊ ምክክሩ የተገኙ ምክረ-ሃሳቦች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ይቀርባሉ - ኢዜአ አማርኛ
ከሀገራዊ ምክክሩ የተገኙ ምክረ-ሃሳቦች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ይቀርባሉ
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ)፦ ከሀገራዊ ምክክሩ የተገኙ ምክረ-ሃሳቦች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሚቀርቡ ምክር ቤቱ ገልጿል።
ከሀገራዊ ምክክር ጉባኤው የተገኙ ምክረ- ሃሳቦች በየፈርጁ እየተደራጁ መሆኑንና በቀጣይ ምክረ-ሃሳቦቹን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሚያቀርብ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
የኮሚሽኑ መግለጫ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፦
ኮሚሽኑ ከሀገራዊ ምክክር ጉባኤው የተገኙ ምክረ-ሃሳቦችን በየፈርጁ በማደራጀት ላይ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከሐምሌ 01 ቀን - ነሐሴ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የሀገራዊ ምክክር ጉባኤውን ሲያስተባብር መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡
በዚህ ሂደት ኮሚሽኑ በርካታ ሀገራዊ ፋይዳ ያላቸውን ምክረ-ሃሳቦች ማሰባሰብ የቻለ ሲሆን ይህም ኢትዮጵያዊያን በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ለመመካከር ያሳዩት ቁርጠኝነት ውጤት ነው፡፡
ኮሚሽኑ በአዋጅ ቁጥር 1265/2014 አንቀፅ 9 (10፣ 11፣ 12) በተሰጠው ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት
የሀገራዊ ምክክር ጉባዔ አጀንዳዎችን፣ የምክክሮቹን ሂደት፣ በምክክሮቹ የተገኙ ምክረ-ሃሳቦችን እንዲሁም ምክረ- ሃሳቦቹ በተግባር ላይ ሊውሉ የሚችሉበትን ሥልት የሚገልጽ ሰነድ በማዘጋጀት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ለአስፈጻሚ አካሉ እና ለሌሎች የሚመለከታቸዉ የመንግስት አካላት አቅርቦ፤ ለሕዝብም ይፋ እንደሚያደርግ፤
መንግሥት ከሀገራዊ ውይይቶች የሚገኙ ምክረ-ሃሳቦችን በተግባር ላይ ለማዋል እንዲችል ግልፅ እና ተጨባጭ የሆነ ዕቅድ እንዲዘጋጅ አስፈላጊውን እገዛ እንደሚያደርግ፤ እንዲሁም
የምክረ-ሃሳቦቹን አፈፃፀም መከታተል የሚያስችል ሥርዓት እንደሚዘረጋ በአዋጁ ተደንግጓል፡፡
ይህንን መነሻ በማድረግ ኮሚሽኑ፦
በአሁኑ ሰዓት ከሀገራዊ ምክክር ጉባኤው የተገኙ ምክረ-ሃሳቦችን በየፈርጁ በማደራጀት ላይ ይገኛል፤
በቀጣይ ምክረ-ሃሳቦቹን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀርባል፤
በመቀጠልም ምክረ-ሃሳቦቹን አግባብነት ባለው መንገድ ለሕዝብ ይፋ ያደርጋል፤
በመጨረሻም ምክረ-ሃሳቦቹን ለአስፈፃሚ በማቅረብ ተፈፃሚነታቸውን ይከታተላል፡፡