የግብርና ዘርፍ ምርታማነት የኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ - ኢዜአ አማርኛ
የግብርና ዘርፍ ምርታማነት የኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ
የግብርና ዘርፍ ምርታማነት የኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ
ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፎች ሁለንተናዊ እና አጠቃላይ የኢኮኖሚ እመርታ በማስመዝገብ ላይ ትገኛለች። በተለይ በግብርና ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ሀገራዊ ምርታማነትን ያሳደገ ውጤት ማስመዝገብ አስችሏል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኢፌዴሪ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ እንደተናገሩት፤ በግብርናው ዘርፍ የተከናወኑ ዋና ዋና ስራዎችን የዘርፉን አመርታ ወደ ላቀ ደረጃ አሻግሯል።
በግብርናው ዘርፍ ከተከናወኑ ተግባራት መካከል በክላስተር ማረስ፣ የማሽንና የመሬት አጠቃቀምን ማስፋፋት፣ ምርጥ ዘር ማቅረብ እና የሰፋፊ መስኖ ግድቦችን መገንባት ተጠቃሽ ናቸው።
ለዚህም ነው የሚታረሰው መሬት መጠን 33 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሄክታር መድረስ የቻለው። በ2017/18 የምርት ዘመን ብቻ 1 ነጥብ 85 ቢሊዮን ኩንታል ምርት መሰብሰብ መቻሉን ከግብርና የተገኘ ማስረጃ ያረጋገጣል።
የግብርናውን ዘርፍ ዘመናዊ በማድረግ የዜጎችን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ተስፋ ሰጪ እመርታዎች እየተመዘገቡ ናቸው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በሀገር ደረጃ ተግባራዊ እየሆነ ያለው የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ አስደናቂ ውጤት እያመጣ ነው። በተለይም በአቮካዶ ምርት ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ከፍተኛ የወጪ ንግድ መሆን ችሏል።
ቀደም ሲል በድርቅ እና በረሃብ ይታወቁ የነበሩ አካባቢዎች አሁን የምርት ማዕከል ሆነዋል።
በቦረና ከፍተኛ የስንዴ ማሳ የተሸፈነ ሲሆን፤ በሱማሌ እና በአፋር ክልሎች ደግሞ ሰፋፊ እርሻዎች በመስፋፋታቸው በጠንካራ ስራ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል ያሳዩ አከባቢዎች ናቸው።
የግብርና ሚኒስትሩ አዲሱ አረጋ በበኩላቸው ስለዘርፉ እድገት ሲናገሩ፤ የሀገሪቷ ግብርና ከሰውና እንስሳት ጉልበት ወደ ሜካናይዜሽን እየተሸጋገረ መሆኑን ገልጸዋል።
ከዚህ ቀደም የነበረውን አነስተኛ የማሽነሪ አጠቃቀም ለመቀየር በወጣው ፖሊሲ መሰረት ከቀረጥ ነፃ ማሽነሪዎችን ማስገባት፣ ለአርሶ አደሮች ብድር ማቅረብ እና የሰው ኃይል ማሰልጠን መቻሉ ለዚህ እንደማሳያ ይጠቀሳል።
ባለፉት ዓመታት የመስኖ አውታሮች በመስፋፋታቸው የመስኖ ሽፋን ከዓመት ወደ ዓመት እያደገ መጥቷል።
የግብርና ሚኒስትሩ አቶ አዲሱ እንደሚሉት፤ አርሶ አደሩ ዘመናዊ የውሃ ቴክኖሎጂዎችን፣ የውሃ ማከማቸት ዘዴዎችን እና ፓምፖችን በመጠቀም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ከማምረት ወደ ሁለት እና ሶስት ጊዜ የማምረት አቅም ላይ መድረሱ ለለውጡ ማሳያ ነው።
ይህ እንቅስቃሴ ግብርናው የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም፣ ክረምት ከበጋ ምርት የሚሰጥ እና የምግብ ዋስትናን እንዲሁም የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ አድርጎታል።
ሽግግርሩ ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር፣ የአርሶ አደሩን ገቢ በማሳደግ እና ሀገራዊ የምርት መጠን እንዲጨምር በማድረግ ረገድ እመርታ ማሳየቱን ነው በማስረጃ ተደግፎ የሚገለጸው።
ኢትዮጵያ ቀደም ሲል በዝቅተኛ ምርታማነት፣ በረሃብ እና በተረጂነት የምትታወቅ ቢሆንም አሁን ግን በትክክለኛ የፖሊሲ አቅጣጫ እና በመደመር እሳቤ ያንን የቆየ ታሪክ ሽራ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ መጻፍ ጀምራለች ሲሉ ተናግረዋል።
ሀገሪቷ በራሷ ጥረት ያመጣችው ይህ የግብርና እመርታ ለአፍሪካ እና ለታዳጊ ሀገራት ትልቅ ምሳሌ መሆን መቻሉን ነው አጽንኦት የሰጡት።
አርሶ አደር ሃይሉ ገልገሎ እና ጅሶ ዋጂ ለዚህ ሕያው ምስክር ናቸው። እነርሱ እንደሚሉት በመንግስት ድጋፍ ከበቆሎ ውጪ ስንዴ፣ ቦሎቄ፣ ጤፍ፣ ሽንኩርት እና ሰሊጥ በስፋት ማምረት መጀመራቸው የለውጥ አብነት ነው።
ቀደም ሲል በአንድ ሄክታር ያገኙ የነበረው አነስተኛ ምርት አሁን በመንግስት በሚቀርብ ምርጥ ዘር በመጠቀማቸው ከሄክታር እስከ 50 እና 55 ኩንታል ማግኘት ችለዋል። ይህም በትክክል ከፍተኛ ለውጥ እንዳመጣላቸው ይናገራሉ።
አርሶ አደር ካሳሁን ዳምጠው እና ሳዲቅ ወለኒኡ አሊ በበኩላቸው፤ በአፋር ክልል የሚገኘው መሬት ማንኛውንም የሰብል ዓይነት መቀበል የሚችል በመሆኑ፣ ያላቸውን መሬት፣ ከብትና የሰው ጉልበት በማስተባበር ማሸላ፣ ሰሊጥ እና ሽንኩርት በስፋት እያመረቱ እንዳለ እማኝነታቸውን ሰጥተዋል።
ግብርናው ተቀይሯል። ለውጥም ተመዝግቧል። በግብርና ዘርፍ እየተመዘገበ ያለው እመርታዊ ለውጥ የአዲስ ምዕራፍ መከፈት አብሳሪ ነው።