ቀጥታ፡

በአማራ ክልል የግብርናውን ዘርፍ ከአምራች ኢንዱስትሪው ጋር በማስተሳሰር ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል

ባህር ዳር፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የግብርናውን ዘርፍ ከአምራች ኢንዱስትሪው ጋር በማስተሳሰር ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ።

ጳጉሜን 1 - "የእመርታ ቀንን" ምክንያት በማድረግ አምራች ኢንዱስትሪዎችና የሰብል ልማት ተጎብኝቷል።

የቢሮው ምክትል ሃላፊ አቶ ቃልኪዳን ሽፈራው በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ግብርናውን  ማዘመንና ግብዓቶችን በወቅቱ ማቅረብ ላይ አተኩሮ እየተሰራ ነው።


 

በክልሉ የመኸር ወቅት ከ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብል እየለማ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከዚህም ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ገልፀዋል።

የግብርናውን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች ግብዓት በስፋት ማቅረብ እንዲቻል ማስተሳሰር ላይ ትኩረት ተሰጥቶ  እየተሰራ መሆኑን  ጠቅሰዋል።

ለአብነትም በተያዘው የመኸር ወቅት ለኢንዱስትሪዎች ግብዓት የሚውል አኩሪ አተር በ400 ሺህ ሄክታር፣ በቆሎ በ700 ሺህ ሄክታር እና ስንዴ ደግሞ በ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ እየለማ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የግብርናን ምርታማነት ለማሳደግ የተፈጠረው ጠንካራ ትስስር በዘርፉ እመርታዊ ለውጥ ለማምጣት ማስቻሉንም ገልጸዋል።


 

የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ተፈሪ ታረቀኝ በበኩላቸው፤ የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግ በመሰረተ ልማትና የሙያ ድጋፍ ከማድረግ ባሻገር የግብርና ግብዓት በጥራትና በብዛት እንዲያገኙ በትብብር  እየተሰራ  ነው።

በክልሉ የኢንዱስትሪዎች ቁጥር እያደገ ቢመጣም ለውጭ ገበያ የሚቀርቡና ተኪ ምርቶችን እንዲያመርቱ በተደረገላቸው ድጋፍ እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል ብለዋል።

አቶ ተፈሪ እንዳሉት በ2018 በጀት ዓመት 174 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት የተሸጋጋሩ ሲሆን ከ3ሺህ 900 በላይ ባለሃብቶችም የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደዋል።

የኢንዱስትሪ ዘርፉ እና የግብርና ትስስር በማጠናከሩ ተጨባጭ ውጤት መታየቱን ገልጸው፣ በቀጣይም ይሄ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። 

የ"ኤም ኤስ፣ ኤ ቢዝነስ" ግሩፕ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ አበረ አበራ በበኩላቸው፤ በባህር ዳር የእንስሳት መኖ ማቀነባበሪያ፣ የምግብ ዘይት እና የከረጢት ማምረቻ ፋብሪካዎችን ገንብተው ወደሥራ ገብተዋል።

በምርቶቻቸው የገበያ ዋጋ ከማረጋጋት ባለፈ ፋብሪካዎቻቸው የአካባቢ ጥሬ እቃዎችን በግብዓትነት በመጠቀም የገበያ አማራጭ እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመዋል።

በጉብኝቱ ላይ የተለያዩ ተቋማት ሥራ ሃላፊዎችና ባለሙያዎች የተሳተፉ ሲሆን የአምራች ኢንዱስትሪዎች እንቅስቃሴና በመኸር ወቅቱ የለማ የበቆሎ ሰብል ተጎብኝቷል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም