ቀጥታ፡

የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ የኢትዮጵያን እመርታ በጽኑ መሠረት ላይ እንዲገነባ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ነው

ደሴ፣ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡-የመደመር መንግሥት የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ የኢትዮጵያን እመርታ በጽኑ መሠረት ላይ እንዲገነባ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑ ተገለጸ። 

በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው  የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግ ተግባራዊ የተደረጉ የፖሊሲ ማዕቀፎች ተኪ ምርትንና የውጭ ምንዛሬን በማሳደግ ተደማሪ አቅም ፈጥረዋል።

በዚህም  የገበያ ዋጋን በማረጋጋት አንዲሁም የውጭ ምንዛሬ መዛባትንና የአቅርቦት ችግሮችን በመፍታት በኩል ውጤት አምጥተዋል። 


 

የአምራች ኢንዱስትሪዎች እመርታን በማስመልከት የኮምቦልቻ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ሥራ አስኪያጅ አቶ አህመድ ሰይድ ከኢዜአ  ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ የኢንዱስትሪውን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች በዘርፉ አመርቂ ውጤት እንዲመዘገብ አድርገዋል። 

በተለይ የ“ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ ተኪና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በማምረት ረገድ እመርታዊ ለውጥ እንዲመዘገብ ማድረጉን ነው የገለጹት።

የመደመር መንግሥት የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ የኢትዮጵያን እምርታ በጽኑ መሠረት ላይ እንዲገነባ የራሱን ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑም አስታውቀዋል 

እንደ ሥራ አስኪያጁ ገለጻ፣ በልዩ የኢኮኖሚ ዞኑ መሠረተ ልማቶች ተሟልተው ባለሀብቶች እንዲሰማሩ በተደረገው ጥረት በዞኑ ተኪና ለውጭ ገበያ የሚቀረቡ ምርቶች በከፍተኛ ደረጃ እያደጉ መጥተዋል። 

በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ 59 ሚሊዮን ብር የሚገመት የሀገር ውስጥ ተኪ ምርቶችን ማምረት እንደተቻለ አስታውሰው፣ ከወጪ ንግድም 20 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ለሀገር በማስገኘት እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል ብለዋል 

ከዚህም ባለፈ በንቅናቄው አማካኝነት የምርት አቅም በማደጉ ከ3 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አዲስ የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉን አቶ አህመድ ሰይድ አብራርተዋል።


 

በልዩ ኢኮኖሚ ዞኑ ከተሰማሩ አልሚዎች መካከል የባቲ ትሪዲንግ ኩባንያ ሥራ አስኪያጅ አቶ መስፍን አያሌው በበኩላቸው፤ በ“ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ ታግዘው የጨርቃጨርቅ ክሮችን ማምረት መጀመራቸውን ገልጸዋል። 

ይህም በገበያው ውስጥ ተወዳዳሪ የምንሆንበትን ትልቅ አቅም ፈጥሮልናል ብለዋል።

መንግሥት የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ለማሳደግ የቀየሳቸው የአሰራርና የሕግ ማዕቀፎች ምርታማነታቸውን እያሳደገው መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በልዩ ኢኮኖሚ ዞኑ የሚገኘው የትራይባስ ኢትዮጵያ ኩባንያ የሰው ሀብት አስተዳደር ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ሻምበል ደሳለው ናቸው። 

በዚህም የወንድ ልብሶችን በጥራትና በብዛት በማምረት ወደ አሜሪካ እና ወደ ሌሎች የውጭ ሀገራት በመላክ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እያስገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ኩባንያው ከውጭ ምንዛሬ ግኝቱ ባለፈ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ማንሰራራት የድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝም አረጋግጠዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም