ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግን ትርፋማ በማድረግ ዘላቂ የሕዝብ ሀብት እንዲሆን የተጀመሩ የሪፎርም ሥራዎች ይጠናከራሉ-አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግን ትርፋማ በማድረግ ዘላቂ የሕዝብ ሀብት እንዲሆን የተጀመሩ የሪፎርም ሥራዎች ይጠናከራሉ-አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)
ሎጎ ሐይቅ፤ ጳጉሜን 1/2018(ኢዜአ)፡-ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግን ተወዳዳሪና ትርፋማ በማድረግ ዘላቂ የሕዝብ ሀብት እንዲሆን የተጀመሩ የሪፎርም ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሆልዲንጉ ቦርድ ሰብሳቢ አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለፁ።
ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ያለፈው በጀት ዓመት የአፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ትውውቅ መድረክ ዛሬ በደቡብ ወሎ ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ተካሂዷል።
ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩና የሆልዲንጉ የቦርድ ሰብሳቢ አብዱ ሁሴን(ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ሆልዲንጉን በመደገፍና በማጠናከር ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚሸጋገር ዘላቂ የሀብትና ጥሪት ምንጭ ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ ነው።
በአደረጃጃት፣ በተሻሻለ አሰራር፣ በጠንካራ ፋይናንስ አሰራር፣ በላቀ ፕሮጀክት አፈጻጸምና በውጤታማ የሪፎርም ትግበራ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
በሰባት የኢንቨስትመንት ዘርፎች 46 ኩባንያዎችን አቅፎ የተቋቋመው ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ኩባንያዎቹ ከነበሩበት ችግር በማውጣት ውጤታማ እንዲሆኑ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
መድረኩም የልማት ድርጅቶች ችግሮችን በመፍታት ነገ ጠንካራ የኢኮኖሚ ተቋም በመሆን ለክልሉም ሆነ ለአገራችን እድገት ሚናቸውን እንዲወጡ ለማድረግ ያለመ መሆኑን አስረድተዋል።
የዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ታደሰ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ሆልዲንጉ ድርጅታዊ አቅሙንና የሰው ሃይሉን በማጠናከር ላይ አተኩሮ ስራውን መጀመሩን አውስተዋል።
አሰራሩን በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማዘመን፣ የአሰራር ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማስፈንና አዳዲስ የኢንቨስትመንት እድሎችን በመፍጠር ተስፋ ሰጭ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል ብለዋል።
ከተመሰረተ በአንድ ዓመት ቆይታው አደረጃጀት በመፍጠር፣ አሰራር በመዘርጋትና በሌሎች ተግባራት አበረታች ውጤት ማስመዝገቡንም ጠቅሰዋል።
የዘመን ኮንስትራክሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታደሰ ግርማ ድርጅታቸው በኮንስትራክሽን ዘርፉ ተወዳዳሪ በመሆን ለትውልድ የሚተላለፍ ሀብት ለመፍጠር እየተንቀሳቀሰ ይገኛል ብለዋል
የጣና ፍሎራ ኩባንያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ጨርቆስ በበኩላቸው በሰጡት አስተያየት ኩባንያው የተለያዩ የአበባ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ እያስገኘ መሆኑን ተናግረዋል።
ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ በስሩ ዘመን ኮንስትራክሽን፣ ዓባይና ፀደይ ባንኮች፣ ጎንደር ብቅል ፋብሪካ፣ ጣና ፍሎራን፣ አምባሰል ንግድ ሥራዎችን ጨምሮ በስሩ 46 ኩባንያዎችን አቅፎ የሚንቀሳቀስ ነው።