ቀጥታ፡

የእመርታ ቀን ኢትዮጵያ ወደ አምራችነትና ራስን ወደ መቻል የምታደርገው መዋቅራዊ ሽግግር እየተበሰረ ነው

አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 1/2018 ዓ.ም (ኢዜአ)፦ ጳጉሜን 1 የእመርታ ቀን ኢትዮጵያ ከተረጅነትና ከልመና አስተሳሰብ ወደ አምራችነትና ራስን ወደ መቻል የምታደርገውን መዋቅራዊ ሽግግር እያበሰረች መሆኑን የሚያሳይ ነው ሲሉ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ገለጹ።

ዛሬ ጳጉሜን 1 ቀን 2018 ዓ.ም "እመርታ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት" በሚል መሪ ቃል "የእመርታ ቀን" በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ይገኛል።

በመርሐ ግብሩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የአጋር ድርጅቶች እና የግሉ ዘርፍ ተወካዮች ተገኝተዋል።


 

የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የእመርታ ቀን አከባበር ኢትዮጵያ ከተረጅነት፣ ከጥገኝነት እና ከልመና አስተሳሰብ ተላቃ ወደ አምራችነትና ራስን ወደ መቻል የምታደርገውን መዋቅራዊና ታሪካዊ ሽግግር የሚያበስር ነው።

ሀገሪቷ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ያላትን አቅም በመጠቀም ያከናወነቻቸውን ዓበይት ተግባራትና ያስመዘገበቻቸውን ሁለንተናዊ ስኬቶች ለማሳየት ያለመ መሆኑንም ገልጸዋል።

በተለይም የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ስኬቶች፣ የግብርና ምርታማነትን በማረጋገጥ ረገድ የተመዘገቡ ድሎች፣ ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ እና በማዕድኑ ዘርፍ የታዩ ዓበይት እመርታዎች የዚሁ ታሪካዊ ሽግግር አካል መሆናቸውን ጠቁመዋል።

ማንሰራራት ማለት ያለፈው ታሪካችን የነበሩትን መልካም እሴቶች ይዞ፣ የነበሩብንን እክሎች በማስተካከልና በዘመናዊ እውቀትና ቴክኖሎጂ በመታገዝ ወደ አዲሱ የከፍታ ምዕራፍ መራመድ ነው ብለዋል።

የእመርታ ቀን "እመርታ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት" በሚል ስናከብር ለኢትዮጵያ ብልፅግና እና ለአዲሱ መንግሥት የልማት አጀንዳዎች ትልቅ ግብዓት እንደሚሆኑ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም