የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻችንን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ምቹ አጋጣሚ ፈጥሮልናል - የኤክስፖ ተሳታፊዎች - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻችንን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ምቹ አጋጣሚ ፈጥሮልናል - የኤክስፖ ተሳታፊዎች
አሶሳ፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻችንን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ምቹ አጋጣሚ ፈጥሮልናል ሲሉ በአሶሳ ከተማ በተካሄደው ኤክስፖ ምርቶቻቸውን ያቀረቡ ተሳታፊዎች ገለጹ።
ከነሃሴ 27/2018 እስከ ጳጉሜን 1/2018 "ከመሸመት ወደ ማምረት" በሚል መሪ ሃሳብ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ አሶሳ ከተማ ሲካሄድ የቆየው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ተጠናቋል።
የኤክስፖው ተሳታፊዎች የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻችንን በማስተዋወቅ ባሻገር ቀጣይነት ያለው የገበያ ትስስር ለመፍጠር የሚያስችል እድል አመቻችቶልናል ብለዋል።
ከተሳታፊዎቹ መካከል አፈወርቅ ዴሬሳ፤ ኤክስፖው ምርቶቻቸው የበለጠ እንዲተዋወቁ ከማድረግ ባለፈ በራስ አቅም የሚመረቱ የውበት መጠበቂያ ውጤቶች ትኩረት እንዲያገኙ አድርጓል ሲሉ ተናግረዋል።
የድርጅታቸው ምርት በአፍሪካ ደረጃ ተወዳዳሪ በመሆን ዕውቅና ማግኘቱን ገልጸው በአካባቢው የሚገኙ የተፈጥሮ ሀብቶችን በመጠቀም ሳሙና፣ ሽቶ እና የተለያዩ አይነቶች የውበት መጠበቂያ ውጤቶችን እያመረቱ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ሌላው የግብርና ውጤቶችን በማቀነባበር በኤክስፖው የተሳተፈው የአሶሳ ግብርና ቴክኒክ ሙያ ማሰልጠኛ ኮሌጅ ሲሆን ኮሌጁ የማር ምርት እና ሌሎች የግብርና የተቀነባበሩ የግብርና ውጤቶችን በማቅረብ ተሳትፈዋል።
በኮሌጁ የእንስሳት እርባታ የትምህርት ክፍል ሀላፊ ዙምራ ሰኢድ፤ ኮሌጁ በተግባር የታገዘ የመማር ማስተማር ስራን ተግባራዊ በማድረግ እሴት የተጨመረባቸውን የግብርና ምርቶች ወደ ገበያ ለማቅረብ እየሰራ ነው ብለዋል።
የዲአርቢ እምነበረድ ፋብሪካ ፋብሪካ የምርት ክፍል ድንበሩ መኮንን በበኩላቸው፤ ፋብሪካው እምነበረድን በተለያዩ ቅርጾች በማዘጋጀት ለገበያ እያቀረበ መሆኑን ገልጸው ኤክስፖው የፋብሪካውን የስራ እንቅስቃሴ ማስተዋወቅ ያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ አመንቲ ገሺ፤ ኤክስፖው በክልሉ እያንሰራራ የሚገኘውን የኢንዱስትሪ ዘርፍ የበለጠ ውጤታማ የሚያደርግ እና ባለሃብቶችን በተለያዩ የልማት ዘርፎች ለመሳብ ያግዛል ብለዋል።
ኤክስፖው በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ሀብቶች ወደ ልማት እየተቀየሩ መሆናቸውን በተግባር ያሳዬ እና በቀጣይ የኢንዱስትሪ ዘርፉን የበለጠ ለመደገፍ የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል።
በቀጣይም የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ዘርፉ የሚጠይቀው መሠረተ ልማት በማሟላት ለዘርፉ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል።