በሲዳማ ክልል የህዝብን የልማት ጥያቄ የመመለሱ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ - ኢዜአ አማርኛ
በሲዳማ ክልል የህዝብን የልማት ጥያቄ የመመለሱ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
ሀዋሳ፣ ነሀሴ 28/2018 (ኢዜአ) በሲዳማ ክልል የሕዝቡን የልማት ጥያቄ የሚመልሱ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ አስታወቁ።
በርዕሰ መስተዳድሩ የሚመራ የክልሉ ከፍተኛ አመራር ቡድን በምስራቃዊና ማዕከላዊ ሲዳማ ዞኖች እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን ተዘዋውሮ ተመልክቷል።
ርዕሰ መስተዳድሩ ደስታ ሌዳሞ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ የሕዝቡን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል።
በምስራቃዊ ሲዳማ ዞን በንሳ ወረዳ ዳዬ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ሥራ ከተማዋን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ እና ተመራጭ እንደሚያደርጋት ገልጸዋል።
የኮሪደር ልማት ሥራው በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንደሚበቃም አክለዋል።
ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚነሱ ጥያቄዎችን ለመመለስ ታስቦ እየተገነባ የሚገኘውን የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ለማጠናቀቅም ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
የልኡካን ቡድኑ የአርቤጎና እና የቡራ ወረዳዎችን የሚያገናኘውና በሎጊታ ወንዝ ላይ እየተገነባ ያለው የባሬ ድልድይ እንዲሁም የቡራ ወረዳ የአስተዳደር ጽሕፈት ቤት ሕንፃ ግንባታ በዚሁ ወቅት ከጎበኙዋቸው የልማት ስራዎች መካከል ይጠቀሳሉ።
የክልሉ መንግሥት የሕዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ እና የልማት ጥያቄዎችን የሚመልሱ ፕሮጀክቶችን እውን የማድረጉ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ርዕሰ መስተዳድሩ ገልጸዋል።
በቡራ ወረዳ እየተገነባ የሚገኘው የአስተዳደር ሕንፃም የመንግሥት አገልግሎትን ምቹና ቀልጣፋ በሆነ መንገድ ለመስጠት እንደሚያስችል ነው ያመለከቱት።
በቡራ ወረዳ ዳለቻ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ባንጫ ባዲሶ በበኩላቸው፣ የአርቤጎና እና ቡራ ወረዳዎችን የሚያገናኘው የባሬ ድልድይ መሠራቱ ቀደም ሲል ወንዙን ለመሻገር ይገጥም የነበረውን ችግር እንዳስቀረላቸው ተናግረዋል።
ወንዙ በሚሞላበት ወቅት በርካቶች ለመሻገር ሲሞክሩ በደራሽ ውኃ ይወሰዱ እንደነበር አስታውሰው፣ የድልድዩ ግንባታ ትልቅ እፎይታ እንደሰጣቸው ገልጸዋል።
ሌላው የአርቤጎና ወረዳ ሚቂቾ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ፌኦ ሲዱ በበኩላቸው፣ የድልድዩ መገንባት ምርቶቻቸውን ወደ ገበያ ለማውጣትና የሚፈልጉትን ሸምተው ለመመለስ ይገጥማቸው የነበረውን ችግር እንደፈታላቸው ገልጸዋል።
በጉብኝቱ ላይ የክልሉ፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሮች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።