ቀጥታ፡

የሸገር ከተማ አስተዳደር አርሶ አደሮችን ማዕከል ያደረገ ዘመናዊ ከተማ ለመገንባት የሚያስችሉ ተግባራት እያከናወነ ነው

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፡- የሸገር ከተማ አስተዳደር ዘመናዊና ውጤታማ ከተማ ለመገንባት በሚያደርገው እንቅስቃሴ አርሶ አደሮችን ማዕከል ያደረጉ ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ የከተማዋ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) ገለጹ።

በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች ሲከበር የቆየው የሸገር ከተማ አስተዳዳር የአርሶ አደሮችን ቀን ዛሬ በፓናል ውይይትና የከተማዋ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮችን እውቅና በመስጠት ዛሬ ተጠናቋል። 


 

ዛሬ በዓድዋ ድል መታሰቢያ አዳራሽ በተካሄደ የፓናል ውይይት "የመደመር መንግሥት እይታ እና የአርሶአደሮች ተጠቃሚነት" በሚል ርዕስ ሰነድ ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን፣ ለሞዴል አርሶ አደሮችም የእውቅናና የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቷል።

የሸገር ከተማ ከንቲባ  ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ፤ በከተማዋ ባለፉት ዓመታት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ አሳታፊ ልማትን ለማስፈንና ውጤታማ የኢኮኖሚ ሽግግር ለማምጣት በተከናወኑ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል።

በተለይም ጠንካራ ከተማን ለመገንባት አርሶ አደሩን ማሰልጠን፣ የከተማ ግብርናን ማዘመንና አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረግ ለሀገር ኢኮኖሚ መሰረት ስለሆነ ጠንካራ ስራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል።

የከተማዋን የኢኮኖሚ ዕድገትና ግንባታ እውን ለማድረግ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ ላይ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።


 

የሸገር ከተማ በአዲስ መልኩ ከመደራጀቱ በፊት በክረምት ወቅት ይለማ የነበረው 50 ሺሕ ሄክታር መሬት ብቻ እንደነበር ያስታወሱት ከንቲባው፣ በአሁኑ ወቅት የማልማት አቅሙን ወደ 95 ሺሕ ሄክታር ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል።

በተጨማሪም ቀደም ሲል ከአንድ ሄክታር መሬት በሽያጭ ወይም በምርት ደረጃ በሰፊው ይገኝ የነበረው 37 ኩንታል አማካይ ምርት፣ በአሁኑ ወቅት ወደ 45 ኩንታል ማደጉን ገልጸዋል።

ለአርሶ አደሩ የሚሰጡ ሥልጠናዎችን፣ የግብዓት አቅርቦትና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ ግብርናውን ከባህላዊ ወደ ዘመናዊ ማሸጋገር ተችሏል ያሉት ከንቲባው፤ ይህም ምርትና ምርታማነትን ከመጨመር ባለፈ አርሶ አደሮች ለገበያ በማቅረብ ሀብት እንዲያፈሩ ማስቻሉን ገልጸዋል።

በሌማት ትሩፋትና በቤተሰብ ብልጽግና ረገድም ተጨባጭ ውጤት መገኘቱን የጠቀሱት ከንቲባው፤ በተለይም የግብርና ሥርዓቱን ወደ እንስሳት እርባታ በማሸጋገር አርሶ አደሩ ይበልጥ ተጠቃሚ እየሆነ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

አክለውም ሸገር ከተማ ከተመሠረተ ወዲህ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የገበያ ትስስርን የሚያጠናክሩ የማዕከላዊ ገበያዎችና የመሠረተ ልማት ዝርግታዎች በመከናወናቸው የሕዝቡ ተጠቃሚነት እየተረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል።

ዛሬ እውቅና ከተሰጣቸው አርሶ አደሮች መካከል የፉሪ ክፍለ ከተማ ነዋሪው አቶ በቀለ ደሜ፣ ሸገር ከተማ እንደ አዲስ ከመደራጀቱ በፊት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ያመርቱ እንደነበርገልጸዋል።


 

ባለፉት ሦስት ዓመታት በተደረገላቸው የስልጠና፣ የቴክኖሎጂና የግብዓት አቅርቦት ድጋፍ በእንስሳት እርባታና በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተው ኑሯቸውን ከማሻሻል ባሻገር ለበርካቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አስታውቀዋል።

አርሶ አደር እንግዳ አርጋው በበኩላቸው፣ በተለይም የመስኖ ድንችና ስንዴን በስፋት በማምረት ከፍተኛ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። 

አስተዳደሩ ከጎናቸው በመቆም አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረጉ ውጤታማ መሆን መቻላቸውንም አስታውቀዋል።

አርሶ አደሮቹ አክለውም፣ በቀጣይ በግብርናው ዘርፍ ተግተው በመስራት ወደ ኢንቨስትመንት ለመሸጋገር ዕቅድ እንዳላቸው በመጠቆም፣ በዚህም ሀገራዊ የኢኮኖሚ እድገት ውስጥ የራሳቸውን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም