ቀጥታ፡

የከተማ ግብርና ዘርፍ የገቢ አቅማችንን ለማሳደግ አግዞናል- በሸገር ከተማ በዘርፉ የተሰማሩ

ሱሉልታ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡- በከተማ ግብርና በመሰማራታቸው  የገቢ አቅማቸው ማደጉን በሸገር ከተማ በዘርፉ የተሰማሩ አርሶአደሮች ተናገሩ፡፡

የሸገር ከተማ አርሶ አደሮች ቀን «ዘመናዊ ገበሬና ዘመናዊ ግብርና ለአጠቃላይ ብልፅግና» በሚል መሪ ቃል በከተማው ሱሉልታ ክፍለ ከተማ በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች እየተከበረ ይገኛል።

አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግም የባዛር እና ኤግዚቢሽን ፕሮግራም የተዘጋጀ ሲሆን፣ የግብርና ምርቶች፣ ማሽነሪዎች፣ የምርት ማሳደጊያ ግብዓቶችና ሌሎችም በበዛሩና ኤግዚቢሽኑ ላይ ለእይታና ሽያጭ ቀርበዋል።

የአርሶ አደሮቹ ቀን አከባበር  ዋነኛ ዓላማም በከተሞች በከተማ ግብርና ዘርፍ በስፋት በመሰማራት በምግብ ራስን ከመቻል ባሻገር፣ ትኩስ የግብርና ምርቶችን በበቂ መጠንና በፍትሐዊ ዋጋ ለገበያ በማቅረብ የኑሮ ውድነትን መቀነስ እና ገበያውን ማረጋጋት እንደሆነም ተገልጿል።

የመርሃ ግብሩ ተሳታፊ አርሶ አደሮች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፣ አስተዳደሩ የከተማ ግብርናን በማስፋፋትና  ዘመናዊና ዘላቂነት ያለው የምግብ ዋስትና ማረጋገጫ ስራዎችን በማከናወን ረገድ እየደገፋቸው እንደሚገኝ ገልጸዋል።

አርሶ አደሮቹ የመንግስትን ድጋፍ መነሻ በማድረግ ምርታማነታቸውን ማሳደጋቸውን ጠቅሰው፣ የተፈጠረላቸውን የገበያ ዕድል በመጠቀምም የግብርና ምርቶቻቸውን በማቅረብ ላይ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።

በተለይም በእንስሳት እርባታ ላይ በመሰማራት ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን የገለፁት አርሶ አደሮቹ፣ የእንስሳት እርባታን በማዘመን ረገድ ትልቅ ስራ እየሰሩ እንደሚገኙ ጠቁመዋል።

ከአርሶ አደሮቹ መካከል በንብ እርባታና ማር ምርት ላይ የተሰማሩት አቶ አበራ ሰቦቃ እንደተናገሩት፣ እየሰሩት ባለው ስራ ተጠቃሚነታቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርታቸውን ለገበያ በማቅረብ ገቢያቸውን እያሳደጉ ነው።

ወደፊትም ሀገር ውስጥ ገበያ ብቻ ከማቅረብ ሳይወሰን ወደ ውጭ የሚላከውን ምርት በማሳደግ ረገድ ድርሻችንን እንወጣለን ብለዋል።

በተመሳሳይ ወይዘሮ አሰገደች ስሜ በእንስሳት ተዋጽኦ አቅርቦት ላይ በማህበር ተደራጅተው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።

 በተፈጠረው የገበያ ትስስር ተጠቃሚ መሆናቸውን የጠቆሙት አርሶ አደሯ፤ ከባለሙያዎችና ከመንግስት ጋር በቅንጅት እየሰሩ እንደሚገኙና በቀጣይም ስራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።

የሸገር ከተማ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ደጃኔ በቀለ በበኩላቸው፤ ከተማዋ ቀደም ሲል ምርት ሳታመርት ከውጭ የምትገዛ እንደነበረች አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ግን በዘመናዊ ግብርና በማምረት ለገበያ ማቅረብ መጀመሯን ገልጸዋል።

በከተማ ደረጃ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ በመፍጠርና ከቴክኖሎጂ ጋር ከማስተዋወቅ አንጻር በተከናወኑት ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም