በጋምቤላ ክልል የእንስሳት ጤና አጠባበቅና ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን የማሳደግ ተግባር ውጤት አስገኝቷል - ኢዜአ አማርኛ
በጋምቤላ ክልል የእንስሳት ጤና አጠባበቅና ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን የማሳደግ ተግባር ውጤት አስገኝቷል
ጋምቤላ፣ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል የእንስሳት ጤናን በመጠበቅና ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት ማስገኘታቸውን የክልሉ ዓሣና እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ።
በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ25 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሊትር በላይ የወተት ምርት መገኘቱን ቢሮው ገልጿል።
የክልሉ እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ክርሚስ ሌሮ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በጋምቤላ ክልል ያለውን የእንስሳት ሀብት ምርታማነት ለማሳደግ የተሻሻሉ ዝርያዎችን የማስራጨትና የእንስሳት ጤና ላይ እየተሰራ ነው።
ይህም ውጤት ማስገኘቱን ገልጸው፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የእንስሳት ሀብት ልማቱን ከሌማት ቱሩፋት መርሃ ግብር ጋር በማስተሳሰር የተሰራው ሥራም ለውጤቱ አስተዋጾ ማድረጉን ተናግረዋል።
ለእዚህም በ2018 በጀት ዓመት 25 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሊትር ወተት፣ ከ12 ሚሊዮን በላይ እንቁላል እና ሌሎች የእንስሳት ተዋጾ ምርት መገኘቱን ጠቅሰዋል።
ቢሮው የእንስሳትን ጤና ለማስጠበቅም ዘመናዊ ላቦራቶሪ የማደራጀትና የእንስሳት ጤና ኬላዎችን ተደራሽ የማድረግ ሥራ መሰራቱን ገልጸዋል።
በተለይም በማጃንግ ዞን ጎደሬ ወረዳ በሰው ሰራሽ ማዳቀል የተጀመሩትን የወተት ላሞች ዝርያ የማሻሻል ሥራዎች በአዲሱ በጀት ዓመትም ወደ ሌሎች ወረዳዎች የማስፋት እንቅስቃሴ መጀመሩን ተናግረዋል።
የተሻሻሉ የእንቁላልና የሥጋ ዶሮዎችን በዘርፉ ልማት ለተሰማሩ አርቢዎች ተደራሽ በማድረግ ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው ብለዋል።
የእንስሳት ሀብት ልማቱን ከሌማት ቱሩፋት ኢንሼቲቩ ጋር ማስተሳሰር ከተጀመረ ወዲህ የባለሃብቱ፣ የአርሶ እና የአርብቶ አደሩ የዘርፉ ተጠቃሚነት ማደጉን ጠቅሰዋል።
ይህም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ከማሳደጉ ባለፈ በከተሞች የዋጋ ንረትን ለማርገብ እያገዘ መሆኑን ጠቁመዋል።
በክልሉ ማጃንግ ዞን ጎዴሬ ወረዳ በተሻሻሉ የወተት ላሞች እርባታ ሥራ የተሰማረው አቶ ቢተውልኝ ግርማ እንዳሉት የተሻሻሉ የወተት ላሞችን በማርባት ወተትና የወተት ተዋጾን ለገበያ በማቅረብ ገቢያቸውን እያሳደጉ ናቸው።
በአሁኑ ወቅት ሥራውን በማስፋት በቀን ከ60 ሊትር በላይ ወተት ለህብረተሰቡ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በዶሮ እርባታ ሥራ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የክንድዬና ጓድኞቹ የዶሮ እርባታ ማህበር ተወካይ አቶ ክንድዬ ጥጋቡ ናቸው።
ማህበሩ የእንቁላልና የሥጋ ደሮዎችን በማርባት በጋምቤላ ከተማና አካባቢው ላሉ ነዋሪዎች በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረበ መሆኑን ገልጸዋል።