የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለወጪ ንግድ ዘርፍ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር አዳዲስ የገበያ መዳረሻዎች በመክፈት አወንታዊ ሚና አለው - ኢዜአ አማርኛ
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለወጪ ንግድ ዘርፍ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር አዳዲስ የገበያ መዳረሻዎች በመክፈት አወንታዊ ሚና አለው
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለኢንቨስትመንትና ለወጪ ንግድ ዘርፎች ምቹ ሁኔታ በመፍጠር አዳዲስ የገበያ መዳረሻዎች በመክፈት አወንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑን በዘርፉ የተሰማሩ ባለሃብቶችና የስራ ኃላፊዎች ገለፁ።
በኢትዮጵያ የሆርቲካልቸር ልማት እና ኤክስፖርት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ፀጋዬ አበበ እንደገለጹት፤ በቀደሙት ዓመታት የነበሩ ቢሮክራሲዎች በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ደረጃ ተቀርፈዋል ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት የኢኮኖሚ ሪፎርም በተካሄደበትና ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታ በተፈጠረበት ወቅት ላይ በመሆናችን የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች በተመቻቸ ሁኔታ እንዲሰሩና ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል።
እንደ ቻይና፣ ህንድ እና የአውሮፓ ሀገራት ያሉ ኢንቨስተሮች በተጨማሪ እንደ ቬትናም ያሉ የሩቅ ምስራቅ ሀገራት ኢንቨስተሮች በተለያዩ ዘርፎች መዋዕለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ እየመጡ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ይህም የተካሄደው የኢኮኖሚ ማሻሻያ ውጤት መሆኑን አብራርተዋል።
በሌላ በኩል የቢኮ አግሮ ኢንዱስትሪ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ታምራት አዱኛ በበኩላቸው፤ ድርጅታቸው በዋናነት የስትሮበሪ ምርቶችን ለመካከለኛው ምስራቅ፣ ለሩቅ ምስራቅ፣ ለአፍሪካና ለአውሮፓ ሀገራት በመላክ ላይ እንደሚገኝ ገልፀዋል።
መንግስት ከማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ጋር ተያይዞ አምርተው ለሚልኩ ድርጅቶች እያደረገ ያለው አበረታች ድጋፍ የበለጠ ለመስራት የሚያስችል ነው ብለዋል።
በተለይም ከውጭ ምንዛሬ አቅርቦት፣ ከብድር ወረቀት አሰራርና ጋር ተያይዞ የባንክ አሰራሩ በጣም የተሳለጠ መሆኑን ተናግረዋል።
ይህ አሰራር ድርጅታቸው እንደ ሲንጋፖርና ታይላንድ ካሉ የሩቅ ምስራቅ አገራት ጋር ያለውን የንግድ ግንኙነት በማጠናከር ወደ አዳዲስ ገበያዎች በቀላሉ እንዲገባ ትልቅ እድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
የሻቫሞ ኤክስፖርት ኃ/የተ/የግ/ማህበር የኤክስፖርት ማናጀር አቶ ታሪኩ ጉተታ እንደተናገሩት፤ በቡና ኤክስፖርት ዘርፍ የአውሮፓ ገበያ በዋናነት ይጠቀስ እንደነበር አስታውሰዋል ።
በአሁኑ ወቅት ግን የአውሮፓ ህብረት ከሚያወጣቸው የንግድ ገደቦችና ህጎች ጋር ተያይዞ አማራጭ ገበያዎችን ማስፋፋት አስፈላጊ መሆኑን ገልፀዋል።
መንግስት አዳዲስና አማራጭ ገበያዎችን ለማስፋፋት የሚያደርገው ጥረት የኤክስፖርት መጠን የሚጨምርና በአንድ ገበያ ላይ ያለንን ጥገኝነት የሚቀንስ በመሆኑ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አብራርተዋል።