ለአዲስ ዓመት በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይኖርና ሕገ ወጥ ግብይትን ለመቆጣጠር ቅድመ ዝግጅት ተጠናቋል - ኢዜአ አማርኛ
ለአዲስ ዓመት በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይኖርና ሕገ ወጥ ግብይትን ለመቆጣጠር ቅድመ ዝግጅት ተጠናቋል
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በመጪው የአዲስ ዓመት በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰትና ሕገ ወጥ ግብይትን ለመቆጣጠር አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ስራ መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ከተማ ንግድ ቢሮ ኃላፊ ሀቢባ ሲራጅ አስታወቁ።
የቢሮ ኃላፊዋ ሀቢባ ሲራጅ የ2019 ዓ.ም አዲስ ዓመት በዓልን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ፣ ለአዲስ ዓመት በዓል ግብይት መሳለጥ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት ተጠናቋል።
የበዓሉ ወቅት ከፍተኛ የገበያ ፍላጎትን መነሻ በማድረግ ሊከሰቱ የሚችሉ የዋጋ ጭማሪ፣ የምርት እጥረትና ሕገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።
ለዚህም የበዓል ገበያን ለማረጋጋት 7 የሰብል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ፣ የፋብሪካ ምርቶች መሸጫ፣ 5 የእንስሳት ቄራ ማዕከላትና 264 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ሳምንቱን ሙሉ አገልግሎት እንደሚሰጡ አስታውቀዋል።
በአዲስ አበባ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽንና በኅብረት ሥራ ማኅበራት ትብብር ጤፍ፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የእርድ እንስሳት፣ ዶሮዎችና እንቁላል፣ የምግብ ዘይትና ሌሎች አስፈላጊ ምርቶች በስፋት ለገበያ እንደሚቀርቡ አስረድተዋል።
በበዓሉ ወቅት ሰው ሠራሽ የምርት እጥረት በሚፈጥሩና ዋጋ በሚጨምሩ ሕገ ወጥ ነጋዴዎች ላይ ቁጥጥር በማድረግ አስፈላጊውን አስተዳደራዊና ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድ አሳስበዋል።
የመጋዘን ፍተሻ፣ የመለኪያ መሣሪያዎች ትክክለኛነት፣ የአገልግሎት ጊዜያቸው ያለፈባቸው ምርቶችን የማረጋገጥና የመቆጣጠር ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አብራርተዋል።
ኅብረተሰቡም በዓሉን ምክንያት በማድረግ በግብይት ሥርዓቱ ላይ አሻጥር በመሥራት የሕግ ጥሰትና ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉ አካላትን ሲመለከት በነጻ ስልክ ቁጥር 8588 ጥቆማ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርበዋል።