ቀጥታ፡

የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂክ ትግበራ በብዙ ዘርፎች ለመጣው እድገት የላቀ አስተዋጽኦ አበርክቷል- ምሁራን

ዲላ ፤ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፡- የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂክ ትግበራ በብዙ ዘርፎች ለመጣው እድገትና ለተመዘገበው ስኬት የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የዘርፉ ምሁራን ገለጹ።

ኢትዮጵያ የዲጅታል 2025 ስትራቴጂክ ትግበራ በስኬት በማጠናቀቅ ወደ ሌላ ምእራፍ በመሸጋገር የዲጅታል 2030 ትግበራ በማከናወን ላይ ትገኛለች።

የስትራቴጂክ ትግበራው በዘርፉ በብዙ መልኩ የሚገለፅ እመርታ የተመዘገበ ሲሆን ለተለያዩ ሴክተሮችም የዲጅታል ትግበራና ማንሰራራት ወሳኝ ምእራፍ የከፈተ ሆኗል።

በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዘርፉ ምሁራን የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂክ ትግበራ በብዙ ዘርፎች ለመጣው እድገትና ለተመዘገበው ስኬት የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል።

የዘርፉ ልማት ከተለያዩ ሴክተሮች ተግባራዊ እንቅስቃሴ ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የሚገናኝ መሆኑን ያነሱት ምሁራኑ በተለይም ትምህርት እና ጤናን ጨምሮ የተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች የሚጨበጥ ውጤት ማምጣት አስችሏል ብለዋል።

በዲላ ዩኒቨርሲቲ የኢንዱስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተር አዲሱ ፍርንጆ  (ዶ/ር)፤ የዲጂታል መሰረተ ልማት ከግንባታ ጀምሮ እሰከ ትግበራ ድረስ በጥቂት አመታት በመንግስት የተከናወነው ስራ እና የመጣው ውጤት አስደናቂ መሆኑን አንስተዋል።

የፋይዳ መታወቂያ፣ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትና ሌሎችም ተያያዥ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች ለዜጎች ፈጣን አገልግሎትና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል ማሳቻሉን አንስተዋል።

የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናም በተለይም ወጣቶች በዘርፉ የካበተ እውቀት እንዲኖራቸውና ብቁ ተወዳዳሪ ሆነው የስራ እድል እንዲፈጠርላቸው ያደረገ መሆኑን አንስተዋል።

የዘርፉ ልማት ለብዙ ሴክተሮች እድገትና ማንሰራራት መሰረት መሆኑን አንስተው በዲጅታል ዘርፍ በጥቂት አመታት የታየው ስኬት የኢትዮጵያን መፃኢ እድል በግልጽ የሚያመላክት መሆኑን አስረድተዋል።

የዩኒቨርሲቲው በርካታ አገልግሎቶች በዲጂታል እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው በዘርፉ የወጣቶችን የፈጠራ አቅም ለማሳደግ በሰው ስራሽ አስተውሎትና በሮቦትክስ ዘርፍ ስልጠና እየተሰጠ ስለመሆኑም ተናግረዋል።

 በዩኒቨርሲቲው የኮምፒዮተር ሳይንስ መምህርና ተመራማሪ እንዲሁም የማህበረሰብ አገልግሎት ዲጂታላይዜሽንና የውጭ ፕሮጀክት ዘርፍ ሃላፊ ሰናይት ሞቲ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ በፋይናንስ ስርዓት፣ በአገልግሎትና ሌሎችም ዘርፎች የፈጠረው አቅም ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።

 የዲጂታል ሥርዓት የአገልግሎት አሰጣጥና የአኗኗር ዘይቤ እየሆነ መምጣቱን አንስተው መልዕክት ከመለዋወጥ ጀምሮ የትኛውንም አገልግሎት ለመስጠትና ለማግኘት ከወረቀት ንክኪ ነጻ የማድረግ ስራ እየተስፋፋ ይገኛል ብለዋል።

የከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም የዲጅታል ትግበራ ማዕከል በመሆን በዘርፉ የማህበረሰቡን ግንዛቤ በማሳደግ የዲጂታል 2030 እውን ለማድረግ እየሰሩ መሆኑን አንስተዋል።

የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ትግበራ በአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና አስተዳደራዊ ዘርፎች ላይ መሰረታዊ እመርታዊ ለውጥ ማምጣቱ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም