ቀጥታ፡

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመኸር እርሻን ውጤታማ ለማድረግ ለግብርና ቴክኖሎጂዎችና ግብዓት ትኩረት ተሰጥቷል

አርባ ምንጭ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመኸር እርሻን ውጤታማ ለማድረግ ለግብርና ቴክኖሎጂዎችና ለግብዓት አቅርቦት ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፣ በክልሉ በመኸር እርሻ ከ230 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች እየለማ ይገኛል።

በመኸር እርሻው የስራስር ተክሎች፣ የጓሮ አትክልት እና ድርቅን መቋቋም የሚችሉ እንደ ካሳቫ እና ማሽላ ያሉ ሰብሎች በስፋት እየለሙ መሆናቸውንም አመልክተዋል

ልማቱ በአረምና ተባይ እንዳይጎዳ ክትትል ከማድረግ ባለፈ ዝናብ አጠር በሆኑ አካባቢዎች ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎች መዘራታቸውን ተናግረዋል።

በክልሉ ጋሞ ዞን ዲታ ወረዳ አርሶ አደር ኦርዛማ ኡርካ ሦስት ሄክታር መሬታቸውን  በስንዴ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የስንዴ ልማቱን በኩታ ገጠም ማከናወናቸው የማሳ እንክብካቤና ቁጥጥሩን  በጋራ ለማድረግ እንዳስቻላቸው ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅትም ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በዞኑ ዳራማሎ ወረዳ ሉና የተቀናጀ የእርሻ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ደመቀ ቶላ በበኩላቸው በ400 ሄክታር ማሳ ላይ በቆሎና የተለያዩ የጓሮ አትክልቶን እያለሙ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ምርታማነታቸውን ለማረጋገጥ ማዳበሪያና ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂ እየተጠቀሙ በመሆኑ አዝመራው በጥሩ ቁመና ላይ ይገኛል ብለዋል።

ለምርትና ምርታማነት የግብርና ባለሙያዎች ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እያደረጉላቸው መሆኑን ጠቅሰዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም