ቀጥታ፡

የባሕር በር ለአገር ደኅንነትና ዕድገት ወሳኝ በመሆኑ ዘላቂ መፍትሔ ማግኘት አለበት-አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ

አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለአገር ደኅንነትና ዕድገት ወሳኝ በመሆኑ በሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገዶች ፈጣንና ዘላቂ መፍትሔ ማግኘት አለበት ሲሉ የቀድሞው የውሃ ሚኒስትር አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ አስታወቁ።

አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የዓባይ ምንጭ ባለቤት በመሆኗ ግብፅና ታሪካዊ ጠላቶቿ በሸረቡት ሀገርን የማዳከም ሴራ ከቀይ ባሕር እንድትገለል ተደርጓል።

ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነቷን ያጣችበት ኢ-ፍትሐዊ ሸፍጥም ሦስት አስርት ዓመታትን ያህል እንደሆነው አስታውሰዋል።

ግብፅ የሀገር ውስጥ ባንዳዎችን በመጠቀም ኤርትራ እንድትገነጠል ያደረገችበት ታሪካዊ ክህደት ያወሱት አምባሳደር ሽፈራው፤ በዚህም ኢትዮጵያ ተፈጥሯዊ ሀብቶቿ የሆኑትን አሰብና ምፅዋን እንድታጣ መደረጉን ገልጸዋል።

ግብፅና የሀገር ውስጥ ባንዳዎች ኢትዮጵያ ከዓለም የምትገናኝባቸውን የባሕር በር መዳረሻ ወደቦች እንድታጣ አድርገዋል ብለዋል።

በሕዝብ ያልተመረጠ መንግሥት ሀገርን በመገንጠል ያለ አንዳች ማስረጃ ኢትዮጵያን ወደብ አልባ የማድረግ ምንም ዓይነት ሥልጣን እንዳልነበረው አስታውሰዋል።

በዚህም የሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን የኢትዮጵያን የባሕር መዳረሻ ወደቦች አሳልፎ በመስጠት በሀገርና ሕዝቦቿ ላይ ታሪክ ይቅር የማይለው በደል መፈጸሙን ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ ከታሪካዊ፣ ሕጋዊ፣ ተፈጥሯዊና መልክዓ ምድራዊ የባሕር በር ባለቤትነቷ ርቃ ልትኖር እንደማትችል አመልክተው፤ እየተመዘገበ ያለው ፈጣን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴና የሕዝብ ቁጥሯም አስገዳጅ ነው ብለዋል።

የባሕር በር ባለቤትነትንም በሰላማዊ፣ ሰጥቶ መቀበል መርህና ዓለም አቀፍ ሕግጋት ጭምር ምላሽ ማስገኘት እንዳለበት አስገንዝበዋል።

በአሁኑ ወቅት መንግሥት በሕዝብ ልብ ውስጥ ተዳፍኖ የቆየውን የኢትዮጵያ የባሕር በር አስፈላጊነት የዓለም ሀገራት እንዲገነዘቡት በማስቻል ስኬታማ የዲፕሎማሲ ሥራ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ በቀይ ባህር ቅርብ ርቀት ላይ የምትገኝ መሆኗን ገልጸው ፤ ጥያቄውም ከጥንታዊ የሀገር ሥልጣኔ እስከ ሕግጋትና ተፈጥሯዊ ድረስ ምክንያታዊ ነው ብለዋል።

በኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ላይ የተፈጸመው በደል ከምክንያታዊነት ወሳኝ የሕልውና ጉዳይ መሆኑም አስረድተዋል።

በቀጣይም በድንበር ተሻጋሪ ወንዞቿ ጎረቤቶቿን ተጠቃሚ የምታደረገው ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነቷም ምላሽ ሊያገኝ የሚገባ የትውልድ ጥያቄ መሆኑን አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም