በመደመር መንግሥት ዕይታ አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት የማድረግ ራዕይ ተጨባጭ ውጤት አምጥቷል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ - ኢዜአ አማርኛ
በመደመር መንግሥት ዕይታ አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት የማድረግ ራዕይ ተጨባጭ ውጤት አምጥቷል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ) ፦በቀጣይ አምስት ዓመታት በዘላቂ የልማት ሥራዎች ላይ አፈፃፀማችንን በማላቅ ሕዝባችን የሰጠንን ሀላፊነት በብቃት መወጣት ይኖርብናል ሲሉ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቀጣይ አምስት ዓመትና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ በየደረጃው ባሉ የከተማ አስተዳደሩ የሥራ ኃላፊዎች ውይይት እየተደረገበት ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ ሕዝባችን ያለፈውን ስትራቴጂያዊ ዕቅድ በሚገባ በመፈጸማችን ለቀጣዩ አምስት ዓመታት በድጋሚ እንድናገለግል ድምፁን ሰጥቶናል።
በመሆኑም በቀጣዩ አምስት ዓመታት በዘላቂ የልማት ሥራዎች ላይ አፈጻጸማችንን በማሳደግ፣ ሕዝባችን የሰጠንን ኃላፊነት በብቃት መወጣት ይኖርብናል ብለዋል።
ከ2019 እስከ 2023 በሚተገበረው የአምስት ዓመቱ ስትራቴጂክ ዕቅድ ላይ ሁሉም አመራር የጠራ ግንዛቤ ኖሮት፣ የከተማዋን የብልጽግና ራዕይ የማሳካት የሕዝብ ኃላፊነት እንዳለበት ገልጸዋል።
ሕዝቡ አምኖ እንደገና እንደመረጣቸው የገለጹት ከንቲባ አዳነች፣ የሥራ ባህላችንን በማሳደግ ለዜጎች የገባነውን ቃል የምንፈጽምበት ነው ብለዋል።
ቀጣይነትን መሠረት ያደረገ የሥራ ባህልን ማሳደግና ያለፉ ድክመቶችን በማረም፣ ጥንካሬዎችን በማስቀጠል የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን ማሳለጥ እንደሚገባ ገልጸዋል።
በዕቅዳችን ላይ ተግባቦት መፍጠርና የተግባባንበትን በብቃት መፈጸም ይጠበቅብናል ብለዋል።
በመደመር መንግሥት ዕይታ አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት የማድረግ ራዕይን በተባበረ ክንድ የማሳካት ተግባር ተጨባጭ ውጤት ማምጣት እንዳስቻለ ገልጸዋል።