ቀጥታ፡

በክልሉ የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው ቀጥለዋል- ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)

ጉንችሬ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሕብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ።

በጉራጌ ዞን ጉንችሬ ከተማ አስተዳደር የተገነቡት የጉንችሬ ጤና ጣቢያ እና የጉንችሬ ብራይት አንደኛ እና ቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተመርቀው ለአገልግሎት በቅተዋል።

ፕሮጀክቶቹን የመረቁት ርዕሰ መስተዳደር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ይገኛሉ።

ለአብነትም ዛሬ ከተመረቁት የጤናና የትምህርት ተቋማት በተጨማሪ የገበያ ማዕከላት እና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ግንባታ መከናወኑን ጠቅሰዋል።

ፕሮጀክቶቹ ለማህበረሰቡ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ የክልሉ መንግስት የህዝብን ፍላጎት ለማሟላት ከምንጊዜውም በላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።

ዛሬ የተመረቁት ፕሮጀክቶች መንግስት የማህበረሰቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የጀመረውን ተግባር እውን ለማድረግ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳያሉ ሲሉም አክለዋል።

ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ እና በእውቀት የታነጹ ምስጉን ተማሪዎችን ለማፍራት በሚደረገው ጥረት ፕሮጀክቶቹ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖራቸውም አመልክተዋል።

በክልሉ የሕብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል ርስቱ ይርዳው የጉንችሬ እና በዙሪያው ያሉ ነዋሪዎች በጤናና በትምህርት ተቋማት እጥረት የተነሳ ሲቸገሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል።

መንግስት ህብረተሰቡንና ረጂ ድርጅቶችን በማስተባበር ያስገነባቸውና ዛሬ ለምረቃ የበቁት ፕሮጀክቶች ይህን ችግር እንደሚፈቱ ጠቅሰው፣ ማህበረሰቡ ፕሮጀክቶቹን ከመጠበቅ ባለፈ ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ የበኩሉን እንዲወጣ አሳስበዋል።

የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ የጤና ተቋሙ እና የትምህርት ቤቶቹ ግንባታ በዞኑ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ገንብቶ የመጨረስ ማሳያ ናቸው ብለዋል።

ፕሮጀክቶቹ የማህበራዊ አገልግሎት ተቋማትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ የልማት ጥያቄን ምላሽ ለመስጠት ማስቻላቸውንም ተናግረዋል።

የጉንችሬ ከተማ ከንቲባ አቶ አብድልቋድር ሂጅራ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የማህበረሰቡን ጤና ለማሻሻል እና ጥራት ያለው ትምህርት ተደራሽ ለማድረግ የፕሮጀክቶቹ መገንባት ትልቅ አስተዋጽኦ አለው።

በፕሮጀክቶቹ የምረቃ መርሀ ግብሩ ላይ የፌደራል፣ የክልል፣ የጉራጌ ዞን እና የጉንችሬ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና ነዋሪዎች ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም