በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ72 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቅባት እህሎች እየለማ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ72 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቅባት እህሎች እየለማ ነው
አምቦ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ72 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቅባት እህሎች በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገልጿል።
ምዕራብ ሸዋ ዞን ለተለያዩ የሰብል አይነቶች ተስማሚ የሆነ የአየር ንብረት እና ለም አፈር ያለው አካባቢ ነው።
ዞኑ ከዋና ዋናዎቹ የጥራጥሬ እና የእህል ዘሮች ባሻገር፣ እንደ ኑግ፣ ተልባ፣ ሰሊጥ እና የጎመን ዘር ያሉ የቅባት እህሎችን በማምረት በኩል ከፍተኛ አቅም አለው።
በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የአዝእርት ልማት ባለሙያ አቶ በላይ በቀለ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በ2018/19 የምርት ዘመን ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውን የቅባት እህሎች በማልማቱ ስራ ላይ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል።
ከለማው ሰፊ መሬት ውስጥ 40 ሺህ 665 ሄክታሩ በሰሊጥ የተሸፈነ ሲሆን፣ ቀሪው መሬት ደግሞ በኑግ፣ በተልባ፣ በጎመን ዘር እና በለውዝ መልማቱን ባለሙያው ገልጸዋል።
ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግም በግብርና ምርምር ማዕከላት የተሻሻሉ የቅባት እህሎች ለአርሶ አደሩ ተሰራጭተው ጥቅም ላይ እየዋሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የቅባት እህል ልማቱ የምግብ ዘይት እጥረትን ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አቶ በላይ ተናግረዋል።
በቅባት እህሎች ልማት 88 ሺህ 761 የዞኑ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ ሲሆን፣ አሁን እየለማ ካለው መሬት 653 ሺህ 535 ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ጠቁመዋል።
በልማቱ ከተሳተፉት መካከል የአምቦ ወረዳው አርሶ አደር ፈይሳ በቀለ በሰጡት አስተያየት፣ በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ ኑግ እንዲሁም በሌላ ግማሽ ሄክታር ላይ ተልባ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ካለሙት መሬት ጥሩ ምርት እንደሚጠብቁ በመግለጽ፣ በአሁኑ ወቅትም ጠንካራ የአረምና የተባይ አሰሳ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን አስረድተዋል።
ሌላው የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር አለማየሁ በሬቻ፣ በመኸር እርሻው በግማሽ ሄክታር ማሳቸው ላይ ተልባና ጎመን ዘር መዝራታቸውን በመግለጽ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።
የቅባት እህል ምርት በገበያ ላይ ከፍተኛ ተፈላጊነት ያለው በመሆኑ፣ ልማቱን ይበልጥ የማስፋፋት እቅድ እንዳላቸው አስረድተዋል።
አርሶ አደሮቹ በግብርና ባለሙያዎች አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገላቸው በመሆኑ፣ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን ባለፈው መኸር ከለማው ከ69 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ከ623 ሺህ ኩንታል በላይ የቅባት እህል ምርት መገኘቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።