በዞኑ 217 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ለምቷል - ኢዜአ አማርኛ
በዞኑ 217 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ለምቷል
ገንዳ ውኃ፣ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን በ217 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውል የአኩሪ አተር ሰብል እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ።
የመምሪያው ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው የመኸር ወቅት የኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃ ፍላጎትን ለማሟላትና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል።
የግብርናው ዘርፍ ለኢኮኖሚ እድገት ያለውን የጎላ አበርክቶ ለማሳደግ ምርታማነትን መጨመር አስፈላጊ በመሆኑ፣ በቂ የግብርና ግብዓት ለአርሶ አደሩ በወቅቱ እንዲሰራጭ መደረጉንም ተናግረዋል።
በአኩሪ አተር ልማቱ 60 ሺህ የሚደርሱ አርሶ አደሮችና ከ600 በላይ አልሚ ባለሃብቶች የተሳተፉ ሲሆን፤ ከልማቱ ከ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ አስረድተዋል።
ጥራቱ የተጠበቀ ምርት ለማግኘት ከዘር ወቅት ጀምሮ በቅድመና ድህረ-ምርት አያያዝ ላይ ሰፊ ክትትልና ቁጥጥር የማድረግ ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ኃላፊው አመልክተዋል።
የምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ገብሬ መልኬ በበኩላቸው፤ በተያዘው የመኸር ወቅት ከ60 ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ማልማት መቻላቸውን ገልጸዋል።
የኢንዱስትሪዎች መስፋፋትና የገበያ ሁኔታው መሻሻል ለአኩሪ አተር ሰብል ልማት ይልጥ ትኩረት እንዲሰጡ እንዳደረጋቸውም ተናግረዋል።
በወረዳው የኮረደም እርሻ ጣቢያ አልሚ አርሶ አደር ምህረቴ ምኒልክ፤ ምርታማነትን በሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎች በመታገዝ አኩሪ አተር እያለሙ መሆኑን ገልጸዋል።
ከግብርና ባለሙያዎች የሚደረግላቸው ሙያዊ ድጋፍና የሚቀርቡ የግብርና ግብዓቶች የሰብሉ ቡቃያ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንዲገኝ ማስቻሉንም አክለዋል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን ባለፈው የምርት ዘመን ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ለምቶ 5 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።