ቀጥታ፡

የስፔሻላይዝድ የውሃ ላቦራቶሪው የውሃ ጥራትን በማስጠበቅ የምርመራና ምርምር አቅም ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ ይኖረዋል

አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የስፔሻላይዝድ የውሃ ላቦራቶሪው የውሃ ጥራትን በማስጠበቅ የምርመራና ምርምር አቅም ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። 

ኢንስቲትዩቱ የውኃ ጥራት ምርመራንና ምርምርን ለማጠናከር የተገነባውን ስፔሻላይዝድ የውኃ ምርመራ ላቦራቶሪ ዛሬ አስመርቋል።


 

የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ታመና ኃይሉ እንደገለጹት፤ የውኃ ጥራትን በተሟላ መልኩ መመርመር የሕዝብ ጤናን ከመጠበቅ ባሻገር የውኃ ሀብትን በዘላቂነት ለመጠቀም የላቀ ሚና አለው።

ላቦራቶሪው የሕክምናና የውኃ ማጣሪያ ሂደቶችን በተገቢው ለመምራትና የሀገሪቱን የምርመራ አቅም ለማሳደግ ወሳኝ መሆኑንም ገልጸዋል።

በተለይም ለመጠጥ፣ ለመስኖና ለኢንዱስትሪ የሚውል ውኃ ተገቢውን የጥራት ደረጃ እንደሚያሟላ ለመለየት ምርመራ የሚያካሂድ ሲሆን፣ የውኃ ምርመራ ውጤቶችን በአንድ ቦታ በማሰባሰብ ለምርምርና ለዕውቀት ማከማቻ ለማዋል ያስችላል ብለዋል።

አንድ የውኃ ምንጭ በአንድ ወቅት ንጹሕ መሆኑ በሌላ ወቅትም ተመሳሳይ ጥራት እንዳለው አያረጋግጥም።

በመሆኑም የውኃ ጥራት በየጊዜው በመመርመር ውጤቶቹ በዳታ መልክ መመዝገብና ለተለያዩ የልማትና የምርምር ሥራዎች መዋል እንዳለበት ጠቁመዋል።

በላቦራቶሪው በኩል በሀገሪቱ በተበታተነ መልኩ የሚገኙ የላቦራቶሪ አቅሞችን በማስተሳሰር፣ ባለሙያዎችን በማሰልጠንና በአይኤስኦ ደረጃዎች የተመሠረተ የምርመራ ሥርዓት በመዘርጋት የሀገሪቱን የላቦራቶሪ አቅም ለማጠናከር እንደሚሠራም ተገልጿል።


 

በኢንስቲትዩት የሥራ አመራር ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጀምበርነሽ ክንፈ በበኩላቸው፣ የውኃ ናሙና እና ምርመራ የሚወጣውን የውጭ ምንዛሬ ለማስቀረት ላቦራቶሪው ወሳኝ ሚና እንዳለው ተናግረዋል።

ላቦራቶሪው ከውኃ ጥራት ምርመራ በተጨማሪ የውኃ ጥራት ምርምርና ሥልጠና እንዲሁም ከአቅም በላይ የሆኑ ምርመራዎችን በማከናወን እንደ ሪፈራል ላቦራቶሪ ሊያገለግል እንደሚችልም አስረድተዋል።

በተጨማሪም የተፋሰስና የምሥራቅ አፍሪካ ሀገራት የውኃ ናሙናዎችን ወደ ኢትዮጵያ በማምጣት እንዲያስመረምሩና ከውኃ ጋር ተያያዥ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ ዕድል እንደሚፈጥርም ጠቁመዋል።

ላቦራቶሪው በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር የውኃ ጥራትን ከማረጋገጥ ባለፈ የምርምር፣ የሥልጠና፣ የገቢ ማመንጫና የውኃ ዲፕሎማሲ ማዕከል ሆኖ ያገለግላል ሲሉም ተናግረዋል።


 

ላቦራቶሪው በውኃ ውስጥ የሚገኙ ኬሚካላዊ፣ አካላዊና ማይክሮባዮሎጂያዊ ይዘቶችን በመመርመር የውኃ ጥራትን ለማረጋገጥ ያግዛል ያሉት ደግሞ የውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የስፔሻላይዝድ ላቦራቶሪ መሪ ሥራ አስፈጻሚ አብዱረህማን ሰይድ ናቸው።

ቀደም ሲል በሀገር ውስጥ ባሉ ላቦራቶሪዎች ሊከናወኑ ያልቻሉ አንዳንድ ምርመራዎች ወደ ውጭ በመላክ ይከናወኑ እንደነበር ጠቁመው፣ የምርመራ ውጤት ለማግኘት የሚወስደውን ጊዜም ያሳጥራል ብለዋል።

በውኃ ውስጥ የሚገኙ ኬሚካሎች ወይም ጎጂ ማይክሮኦርጋኒዝሞች ከተፈቀደው መጠን በላይ መኖራቸው በሰው ጤና ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ሊያሳድር ስለሚችል፣ የውኃ ጥራትን በላቦራቶሪ መፈተሽ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም