ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም የቻይና ባለሀብቶችን ይበልጥ እየሳበ ነው-አምባሳደር ቼን ሃይ

አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና እየተሻሻለ የመጣው የኢንቨስትመንት ከባቢ ይበልጥ የቻይና ባለሀብቶችን እየሳበ እንደሚገኝ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ ገለጹ።

አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ግዙፍና ፈጣን እድገት ካላቸው ኢኮኖሚዎች አንዷ መሆኗን ገልጸዋል።

ሀገሪቱ ለዓለም አቀፍ የንግድ አጋሮችና ባለሀብቶች ሰፊ የኢንቨስትመንት እድሎችን እያቀረበች እንደምትገኝም አመልክተዋል።

አምባሳደሩ የኢንዱስትሪ ልማት፣ የከተሜነት መስፋፋት እና የግብርና ዘመናዊነት አሰራሮችን ጨምሮ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ቁልፍ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ዘርፎች እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶችን አድንቀዋል።

በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው እያደገ የመጣው የኢኮኖሚ ትስስር ለሀገራዊ ዕድገት አስተዋጽኦ ከማበርከት ባለፈ፣ የማህበረሰቡ ኑሮ እንዲሻሻል መልካም አጋጣሚ መፍጠሩን አንስተዋል።

ቻይናና ኢትዮጵያ ሀገራዊ ዕድገትና የመዘመን ራዕይን እውን ለማድረግ የጋራ የሆነ መሻት እንዳላቸውም አብራርተዋል።

አምባሳደሩ ባለፉት ሁለት ዓመታት በኢትዮጵያ በቆዩበት ጊዜ በሀገሪቱ የኢኮኖሚ ምህዳርና የንግድ ከባቢ ላይ ግልጽ ለውጦች እንደተመለከቱም ተናግረዋል።

በዚህም የቻይና ባለሀብቶችና ሥራ ፈጣሪዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ጠቅሰው፣ አዳዲስ ፋብሪካዎችና ማምረቻዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን አንስተዋል።

የኢንቨስትመንት ከባቢው እንዲሻሻል በፌዴራልና በክልል መንግሥታት የተደረጉ ማሻሻያዎች ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት አምባሳደሩ፣ እነዚህ እርምጃዎች ለንግድና ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እንዳስቻሉም አክለዋል።

በተጨማሪም በኢትዮጵያና በቻይና መካከል ያለው የንግድ ግንኙነት እየሰፋ መሄዱን፣ በተለይም የቻይና ሸማቾች ለኢትዮጵያ ምርቶች ያላቸው ፍላጎት እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል።

እንደ ቡናና ሰሊጥ ያሉ የኢትዮጵያ የግብርና ምርቶች በቻይና ገበያ ያላቸው ተወዳጅነት ማደጉን ጠቅሰው፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የኢንዱስትሪና እሴት የተጨመረባቸው ምርቶችም ጭምር በቻይናውያን ሸማቾች ዘንድ ሰፊ ተቀባይነት እያገኙ መምጣታቸውን አመልክተዋል።

አምባሳደሩ በቻይና ንግድ ተቋማትና በኢትዮጵያ መንግሥት አካላት መካከል በቀጣይ የሚኖረው ትብብር የሀገሪቱን የንግድ ምህዳር ይበልጥ እንደሚያጠናክረውና ለንግድና ኢንቨስትመንት ሰፊ ዕድሎችን እንደሚፈጥር ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።

የንግድና ኢንቨስትመንት ጠንካራ ትብብር የሁለቱን ሀገራት ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከማፋጠን ባለፈ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ይበልጥ እንደሚያጎለብተውም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያና የቻይና ግንኙነት በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂክ አጋርነት (all-weather strategic partnership) ደረጃ ከፍ ማለት፣ የሁለቱን ሀገራት ለሰፊ ትብብርና ለጋራ ልማት ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚያሳይና የቻይና-አፍሪካን የኢኮኖሚ ግንኙነት አጠቃላይ ፋይዳ አጉልቶ የሚያሳይ መሆኑንም ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም