ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ያመጣቻቸውን ለውጦች ለሀገራት አካፈለች - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ያመጣቻቸውን ለውጦች ለሀገራት አካፈለች
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ዲጂታላይዜሽንና ሰው ሰራሽ አስተውሎትን ለተሻለ የህክምና ውሳኔ አሰጣጥ በመጠቀም ያመጣቻቸውን ለውጦች ለአፍሪካ ሀገራት ማካፈል መቻሏን የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ ገለጹ።
ኢትዮጵያ ዲጂታላይዜሽንና ሰው ሰራሽ አስተውሎትን ለተሻለ የህክምና ውሳኔ አሰጣጥ በሰፊው እየተጠቀመች መሆኑንም ገልጸዋል።
በአምስት የጤና ዘርፍ ምሰሶዎች ላይ በማተኮር ለአራት ቀናት የሚቆየው 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል።
የመድረኩ ዋና ዋና የጤና ምሰሶዎች ዘላቂ የጤና ፋይናንስና የዲጂታል ጤና ሥርዓት፣ የመጀመሪያ ደረጃ የጤና ክብካቤ፣ እንዲሁም የጤና ባለሙያዎችና የሀገር ውስጥ ምርቶች አቅም ማሳደግ ናቸው።
በዛሬው እለትም የጉባኤው አካል የሆነ በጤናው ዘርፍ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ሚና በሚል በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የመሰብሰቢያ አዳራሽ ውይይት ተካሂዷል።
ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ በርካታ የዲጂታላይዜሽንና የሰው ሰራሽ አስተውሎት ውጤቶችን እየተጠቀመች መሆኑን ገልጸዋል።
በዚህም ለህክምና ውሳኔ አሰጣጥ ጥቅም ላይ ይውሉ የነበሩ የወረቀት አሰራሮች በዲጂታል መተካታቸውን ገልጸው በመድረኩ ኢትዮጵያ ተሞክሮዋን አካፍላለች ብለዋል።
እንዲሁም ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት የተደገፈ የጤና ኤክስቴንሽን ፐሮግራም እየተገበረች መሆኑንና ይህንንም ተሞክሮ ማካፈሏን ጠቁመዋል።
በሰው ሰራሽ አስተውሎት የተደገፈው የጤና ኤክስቴንሽን ፕሮግራም በአምስት ቋንቋ ከአንድ መቶ በላይ መመሪያዎችን ባለሙያዎች በስልክ እንዲያገኙ ማስቻሉን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በራስ የሚሰሩ እና የሚተዳደሩ ዲጂታል ቴክኖሎጂዎች ጥቅም ላይ ማዋሏን አንስተው ለረጅም ጊዜ በተበታተነ መንገድ አገልግሎት ይሰጡ የነበሩ ሲስተሞች ወደ አንድ ማምጣት መቻሉንም አክለዋል።
በዚህም በጤናው ዘርፍ ከፍተኛ እመርታ መመዝገቡንና አገልግሎት አሰጣጡንም ማቀላጠፉን ሚኒስትር ዴኤታዋ ጨምረው ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ አገልግሎት ላይ የዋሉ የዲጂታላይዜሽንና የሰው ሰራሽ አስተውሎት ውጤቶች በህክምና ውሳኔ አሰጣጥ ውጤታማነት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽአ እያበረከቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
እነዚህ ጥቅም ላይ የዋሉ ቴክኖሎጂዎች በዘርፉ የተጠቃለሉ መረጃዎችን ለውሳኔ ሰጭ አካላት ማቅረብ እያስቻሉ መሆኑንና አጠቃላይ በጤና ስርዓቱ ላይ ትልቅ አቅም እየፈጠሩ እንደሚገኙ አመላክተዋል።