በጋምቤላ ክልል የልማት አቅሞችን ለይቶ ተግባራዊ የማድረግ ስራ ቀዳሚ ትኩረት ይሰጠዋል-ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ - ኢዜአ አማርኛ
በጋምቤላ ክልል የልማት አቅሞችን ለይቶ ተግባራዊ የማድረግ ስራ ቀዳሚ ትኩረት ይሰጠዋል-ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 20/ 2018 (ኢዜአ) ፡-የጋምቤላ ክልል ሕዝብን የኑሮ ደረጃ በዘላቂነት ለማሻሻል በየዘርፉ ያሉ የልማት አቅሞችን አውጥቶ ተግባራዊ የማድረግ ስራ ቀዳሚ ትኩረት እንደሚሰጠው ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ።
የቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት በጋምቤላ ክልል በሚገኙ ዘጠኝ ወረዳዎች በአዲሱ በጀት ዓመት ለሚያስፈጽማቸው የልማት ስራዎች የሚሆን ከ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት በክልሉ ስቲሪንግ ኮሚቴ አጽድቋል።
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ ወደ ክልሉ የሚመጡ አጋዥ የልማት ፕሮጀክቶችን ከልማት እቅዶች ጋር አጣጥሞ በመተግበር የህዝቡን ህይወት ለመለወጥ በትኩረት መስራት ይገባል።
በክልሉ እየተተገበረ ያለው የቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት ባለፉት ዓመታት ባከናወናቸው የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎች ህዝቡን ተጠቃሚ ማድረጉንም ገልጸዋል።
አክለውም በዘንድሮው በጀት ዓመት በትምህርት፣ በግብርና፣ በመንገድና በሌሎች የኑሮ ማሻሻያ ዘርፎች የታቀዱት ስራዎች የህዝቡን ህይወት ሊያሻሽሉ የሚችሉ መሆናቸውን አስገንዝበዋል።
ለፕሮጀክቶቹ ስኬታማነት የስትሪንግ ኮሚቴውና የሌሎች ባለድርሻ አካላት ድጋፍ፣ ትብብርና ቅንጅታዊ አሰራር ሊጎለብት እንደሚገባ አመልክተው ለዚህም የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
የፕሮጀክቱ የጋምቤላ ክልል አስተባባሪ ዶክተር ቤል ቢቾክ በበኩላቸው፣ ፕሮጀክቱ ባለፉት ዓመታት የማህበረሰቡን ኑሮ የሚለውጡ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን ገልፀዋል።
በዘንድሮው በጀት ዓመትም ተመሳሳይ ተግባራትን ለማከናወን ከ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ በመመደብ ወደ ተግባር ምዕራፍ መግባቱን ተናግረዋል።
በበጀት ዓመቱ 35 የትምህርት ቤት፣ የእንስሳት ጤና ኬላ፣ የመንገድ ግንባታና ዲዛይን እንዲሁም ሌሎች የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ ፕሮጀክቶች እንደሚከናወኑ ጠቁመዋል።
ለእነዚሁ ተግባራት ስኬትም የባለድርሻ አካላትን ድጋፍና ትብብር እንደሚያስፈለግ ነው የተናገሩት።
የቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት በመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ስር በሰባት ክልሎችና በአንድ ከተማ አስተዳደር በሚገኙ 120 ወረዳዎች የማህበረሰቡን ኑሮ ለማሻሻል እየተተገበረ የሚገኝ መሆኑ መረጃ ያመለክታሉ ።