በድሬዳዋ አስተዳደር ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ ልማትን ለማቀላጠፍ ቅንጅታዊ ሥራ ተግባራዊ ተደርጓል - ኢዜአ አማርኛ
በድሬዳዋ አስተዳደር ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ ልማትን ለማቀላጠፍ ቅንጅታዊ ሥራ ተግባራዊ ተደርጓል
ድሬዳዋ፣ነሐሴ 20/2018(ኢዜአ)፡-በድሬዳዋ አስተዳደር ገቢን በአግባቡ ሰብስቦ ልማትን ለማቀላጠፍ ቅንጅታዊ ሥራ ተግባራዊ መደረጉን የአስተዳደሩ ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አብዱልሰላም መሐመድ (ዶ/ር) ተናገሩ ።
በዘንድሮ በጀት ዓመት በአስተዳደሩ 15 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ቅንጅታዊ እንቅስቃሴዎች መጀመራቸው ተመላክቷል።
የድሬዳዋ ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አብዱልሰላም መሐመድ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ አስተዳደሩ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢን በአግባቡ ለመሰብሰብ የግብር ከፋዮችን ግንዛቤ ከማሳደግ ባለፈ በቴክኖሎጂ ታግዘው ግብራቸውን በመክፈል ግዜና ገንዘባቸውን እንዲቆጥቡ እያደረገ ነው።
የከተማዋ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል።
በዚህም በበጀት ዓመቱ ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች እንዲሁም ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች 15 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ሥራው ተጀምሯል ብለዋል።
ስራውንም በንቅናቄ በመምራት ሐምሌ ወር ብቻ ከ934 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ከ890 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡን ጠቁመዋል።
በእዚህም የዕቅዱን ከ95 በመቶ በላይ ለማሳካት እንደተቻለና ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ685 ሚሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለው አመልክተዋል።
በሚሰበሰብ ገቢም የህዝብ የመንገድ፣ የንፁህ መጠጥ ውሃ፣ የአነስተኛ መስኖ አውታሮች፣ የኮሪደር ልማት እና ሌሎች የመሠረተ ልማት ሥራዎችን በማስፋፋት የነዋሪውን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ይሰራል ብለዋል።
በድሬዳዋ ገቢዎች ባለስልጣን ግብራቸውን በመክፈል ላይ ከነበሩት መካከል ወይዘሮ ሂዩስቲና ስዩም እና አቶ ዮሴፍ አለባቸው ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በባለስልጣኑ የተዘረጋው ቀልጣፋ አገልግሎት ግብራቸውን በወቅቱ ለመክፈል አግዟቸዋል።
የሚከፍሉት ግብር ለድሬዳዋ ዕድገት እና ለነዋሪው ተጠቃሚነት እንደሚውል በማመን ግብራቸውን በወቅቱና በታማኝነት መክፈላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።