ቀጥታ፡

ከከተማዋ የዕድገት ፍጥነት ጋር የሚመጣጠን የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ማከናወን ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦ ከመዲናዋ የዕድገት ፍጥነት ጋር የሚመጣጠን የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ማከናወን የከተማ አስተዳደሩ ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።

ከንቲባ አዳነች አቤቤ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የተገነቡ የተቀናጁ የትራንስፖርት ተርሚናሎች፣ የመኪና ማቆሚያዎችና የገበያ ማዕከላትን መርቀው ስራ አስጀምረዋል።


 

በምረቃ መርሃ ግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ቡዜና አልከድር፣ በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ከተማ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይን እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዲዛይንና ግንባታ ሥራዎች ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር አያልነሽ ሐብተማሪያምን ጨምሮ ሌሎች የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ ከከተማዋ የዕድገት ፍጥነት ጋር የሚመጣጠን የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ማከናወን የከተማ አስተዳደሩ ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫ ነው።

ዛሬ የተመረቁት መሰረተ ልማቶችም በከተማዋ የትራንስፖርት አገልግሎትን ለማዘመንና የትራፊክ መጨናነቅን ለመቅረፍ አይነተኛ ሚና ይኖራቸዋል ብለዋል።

አዲሶቹ የትራንስፖርት ተርሚናሎችና የመኪና ማቆሚያዎች የከተማዋን የትራፊክ ፍሰት ለማቃለል እንዲሁም ምቹ የእግረኛ መንገዶችን ለመፍጠር ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ገልጸዋል።


 

መሰረተ ልማቶቹ መንገድ ዳር የሚቆሙ ተሽከርካሪዎችን በማስቀረት የከተማዋን የትራፊክ መጨናነቅ እንደሚቀንስም ከንቲባዋ አመላክተዋል።

በመኪና ማቆሚያዎቹና ተርሚናሎቹ ውስጥ የዲጂታል ክፍያና የደህንነት ካሜራዎችን ጨምሮ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች መገጠማቸውን ጨምረው አስታውቀዋል።

ፕሮጀክቶቹ በተያዘላቸው ጊዜና ጥራት ተጠናቅቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ ሚናቸውን የተወጡ አካላትን አመስግነው
ህብረተሰቡም የተገነቡ ዘመናዊ የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶችን በአግባቡ እንዲጠቀም አስገንዝበዋል።


 

የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶቹ የተገነቡት በቦሌ ኖክ፣ በየካ፣ በቀበና እና በጎተራ ሲሆን በውስጣቸው የገበያ ማዕከላትን ጭምር ያካተቱ ናቸው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም