በሐረሪ ክልል በኢንቨስትመንት ዘርፍ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ውጤታማ እያደረገን ነው -ባለሀብቶችና ወጣቶች - ኢዜአ አማርኛ
በሐረሪ ክልል በኢንቨስትመንት ዘርፍ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ውጤታማ እያደረገን ነው -ባለሀብቶችና ወጣቶች
ሀረር፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በሐረሪ ክልል በኢንቨስትመንት ዘርፍ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ውጤታማ እያደረጋቸው መሆኑን ባለሀብቶችና ወጣቶች ገለጹ።
በክልሉ ያለው የኢንቨስትመንት አማራጭ ከከፍተኛ ትምህርት ለተመረቁ ወጣቶች የስራ እድል እየፈጠረ መሆኑ ተመላክቷል።
ባለሀብቶችም የክልሉ መንግስት የኢንቨስትመንት ዘርፉን ለማበረታታት በሚያከናውነው ተግባራት በዘርፉ ውጤታማ እያደረጋቸው መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል።
በሀረር ከተማ በኢንቨስትመንት ከተሰማሩ ባለሀብቶች መካከል የሀምዲ ሜዲካል ሰርጂካል ሴንተር ባለቤትና ስራ አስኪያጅ ዶክተር ኑረዲን አህመድ እንደገለጹት የክልሉ መንግስት መሬት ከመስጠት ጀምሮ የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ለኢንቨስትመንት ስራቸው ምቹ ሁኔታን ፈጥሮላቸዋል።
አሁን ላይ የግንባታ ስራቸውን ከ90 በመቶ በላይ ማጠናቀቃቸውን ጠቁመው በቀጣይ ስድስት ወራት ወደ ተሟላ ስራ እንደሚገቡ አመላክተዋል።
በግንባታው ለበርካታ ሰዎች የስራ እድል መፈጠሩን ተናግረዋል።
የክልሉ ኢንቨስትመንት ቢሮ እያደረገላቸው ባለው ድጋፍ ግንባታውን በፍጥነት እያጠናቀቁ መሆናቸውን ገልጸዋል ።
በሐረር ከተማ በሆቴልና ቱሪዝም ዘርፍ ኢንቨስትመንት ላይ መሰማራታቸውን የገለጸው ደግሞ በከተማው የሐረር ፓላስ ሆቴል ስራ አስኪያጅ ወጣት ሔኖክ ተስፋዬ ነው።
የክልሉ መንግስት ከግንባታ ጀምሮ እስካሁን አስፈላጊውን ድጋፍ ሲያደርግላቸው በመቆየቱ ግንባታውን በፍጥነት አጠናቀው ወደ ስራ በመግባት ውጤታማ መሆናቸውን ገልጿል።
ከደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ በመካኒካል ምህንድስና የተመረቀው ወጣት ይስሃቅ ደሳለኝ በክልሉ በኢንቨስትመንት ዘርፍ የሚካሄዱ ግንባታዎች ለተመራቂ ተማሪዎች የስራ እድል እየፈጠሩ መሆናቸውን ተናግሯል።
በክልሉ በግንባታ ላይ በሚገኘው የዘይት ፋብሪካ በተመቻቸለት የስራ እድል አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችና አሰራሮች ጋር በመተዋወቅ እውቀቱን እያዳበረ መሆኑን ገልጿል።
የሐረሪ ክልል ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ምክትል ሃላፊ ሀምዲ ሰለሃዲን እንደገለጹት ባለፉት ዓመታት በክልሉ የኢንቨስትመንት ልማት ላይ የተከናወኑ ተግባራት አበረታችና መነቃቃትን የፈጠሩ ናቸው።
ባለፉት አምስት ዓመታት ከ20 ቢሊየን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በኢንቨስትመንት ዘርፍ ፈቃድ መውሰዳቸውን ተናግረዋል።
የክልሉ መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፉ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው ወደ ኢንቨስትመንት የገቡ ባለሀብቶችም ወደ ምርትና አገልግሎት እንዲገቡ እየተደረገ ያለው ክትትልና ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቀዋል።