የመገጭ ግድብ የመደመር መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅም ማሳያ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የመገጭ ግድብ የመደመር መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅም ማሳያ ነው
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦የመገጭ ግድብ የመደመር መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅም ማሳያ መሆኑን የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ገለጹ።
የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የመገጭ ግድብ ግንባታ ያለበትን ደረጃ ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ተቋማት ለተውጣጡ ጋዜጠኞች አስጎብኝቷል።
የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ጉብኝቱን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፤የመገጭ ግድብ የጎንደር ከተማ የዘመናት ጥያቄ መሆኑን ገልጸዋል።
የመገጭ ግድብ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ለሕዝቡ ያልተሠራውን ተሠራ እየተባለ 18 ዓመታትን ማስቆጠሩን ጠቅሰዋል።
መገጭ ለንጹህ መጠጥ ውሃና ለመስኖ ልማት በመዋል ለኢትዮጵያ ብዙ ጥቅም ማስገኘት የሚችል ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል።
ነገር ግን ፕሮጀክቱ በአግባቡ ባለመመራቱ፣ በጋ ላይ የተሠራው ክረምት ላይ በጎርፍ እየተናደ ለአካባቢው ማኅበረሰብ የሕልውና ሥጋት፣ ለጣና ሐይቅ ደግሞ በደለል መሞላት ምክንያት ሆኖ ቆይቷል ብለዋል።
ይሁን እንጂ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር ሰጭነት ፕሮጀክቱን እንደገና በማጥናት ሕዝብ ከባዶ ተስፋ ወደሚጨበጥ ሕልም ማምጣት እንደተቻለ ገልጸዋል።
ይህም ለሕዝቡ ከሚሰጠው ቀጥተኛ ጥቅም ባለፈ፣ ዓባይ ወንዝና ጣና ሐይቅን ከደለል በመታደግ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት እንዳለው በተግባር ገልጧል ብለዋል።
በመገጭ ግድብ ግንባታ የታየው ፈጣን የግንባታ ለውጥ የመደመር መንግሥት ፕሮጀክት ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅሙን በተግባር ያሳየበት መሆኑን ገልጸዋል።
የመገጭ ግድብ ሰፊ የእርሻ መሬት ላለው የደንቢያ አካባቢ የልማት ተስፋ፤ ለጎንደር ከተማ ደግሞ የዘላቂ ንጹህ መጠጥ ውሃ ብስራት ይሆናል ብለዋል።
ሕብረተሰቡ የግድቡን አስፈላጊነት በወጉ በመረዳት አካባቢውን በንቃት እየጠበቀ፣ የፕሮጀክቱን አፈጻጸም በቅርበት እየተከታተለው መሆኑን ገልጸዋል።
ለ18 ዓመታት ሕዝቡን በባዶ ተስፋና በጎርፍ ሲያማርር የነበረው የመገጭ ግድብ፣ ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግንባታው ተጠናቆ በቅርቡ ይጠናቀቃል ብለዋል።