የማዕድን ዘርፉን የወጪ ንግድ ከማሳደግ ባለፈ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት የመተካቱ ስራ ይጠናከራል - ኢዜአ አማርኛ
የማዕድን ዘርፉን የወጪ ንግድ ከማሳደግ ባለፈ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት የመተካቱ ስራ ይጠናከራል
ሃዋሳ ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ) ፦ በበጀት ዓመቱ የማዕድን ዘርፉን የወጪ ንግድ ገቢ ከማሳደግ ባለፈ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት የመተካቱ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የማዕድን ሚኒስቴር አስታወቀ።
በማዕድን ሚኒስቴር የማዕድን ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ አቶ ብርሃኔ ያዴሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ከአምስቱ ዋና ዋና የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ ከሆነው የማዕድን ዘርፍ ኢትዮጵያ ተገቢውን ጥቅም እንድታገኝ የተከናወኑ የለውጥ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል።
ዘርፉ የሚያስገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ በተደረገ ተቋማዊ ሪፎርም የማዕድን መረጃዎችን በዘመናዊ መልክ በማደራጀት መረጃን መሠረት ያደረገ የማዕድን አመራር ሥርዓት ተዘርግቷል ብለዋል።
የማዕድን ፍለጋዎችንና ሳይንሳዊ ሥራዎችን ከማጠናከር ባለፈ፣ ማበረታቻዎችንና ምቹ መደላድሎችን በመፍጠር ዘርፉ የኢኮኖሚው ሞተር እንዲሆን የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውንም ገልጸዋል።
በመሆኑም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመትም በሀገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውን 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር የወጪ ንግድ ገቢ ከማዕድን ማግኘት ተችሏል ብለዋል።
በተያዘው በጀት ዓመትም ከወርቅ በተጨማሪ በተመረጡ የማዕድን ዘርፎች ላይ በማተኮር የዘርፉን የወጪ ንግድ ገቢ 6 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ግብ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።
ወርቅ ላይ ብቻ የተንጠለጠለውን የወጪ ንግድ ገቢ ለማስፋት፣ ዓለም አቀፍ ፍላጎትን መሠረት በማድረግ በጌጣጌጥና በሌሎች የተመረጡ ማዕድናት ላይ በማተኮር ገቢን የማሳደግና ዘላቂነትን የማረጋገጥ ሥራዎች ይከናወናሉ ብለዋል።
በተኪ ምርት ረገድም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ከውጭ የሚገቡ ማዕድናትን በሀገር ውስጥ የመተካት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፣ አንዳንድ ተኪ ምርቶችን ወደ ውጭ የመላክ ዕቅድ የተያዘበት ዓመት መሆኑንም ገልጸዋል።
የሲዳማ ክልል ማዕድንና ኢነርጂ ኤጀንሲ ሥራ አስኪያጅ አቶ መስፍን መጩካ በበኩላቸው፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የማዕድናት ልየታ ሥራ በትኩረት መከናወኑን ገልጸዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 1 ሺህ 350 ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ መግባቱንና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ከ11 ሺህ ቶን በላይ ማዕድናት ለማዕከላዊ ገበያ መቅረባቸውን ተናግረዋል።
በኮንስትራክሽን ማዕድናትም የሕብረተሰቡን ፍላጎት የሚያሟሉ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት የሚያስችሉ የማርብልና ግራናይት ማዕድናት ወደ ምርት የማስገባት ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል።
በክልሉ በጥናት የተለዩ ከ22 በላይ ማዕድናት መኖራቸውን የገለጹት ደግሞ በኤጀንሲው የማዕድን ሀብት ዳይሬክተር ወ/ሮ ምርትነሽ መኮንን ናቸው።
ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግም በወርቅ፣ ኮንስትራክሽንና ኢንዱስትሪ ማዕድናት ላይ የተሰማሩ ከ320 በላይ ማኅበራት የገበያ ትስስር እንደተፈጠረላቸው ገልጸዋል።
በማርብልና ግራናይት የኢንቨስትመንት ፈቃድ ተሰጥቶ ወደ ምርት ለመግባት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።