አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ መጥቷል- አርሶ አደሮች - ኢዜአ አማርኛ
አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ መጥቷል- አርሶ አደሮች
መተማ፣ ነሐሴ14/2018 (ኢዜአ):- አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን የምዕራብ ጎንደር ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ።
በዞኑ የቆላ ፍራፍሬ ልማትን በኩታ ገጠም አሠራር በሰፊው በማልማት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል።
አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ መጥቷል።
በዞኑ የመተማ ወረዳ አርሶ አደር ደሴ ባይተኩስ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መምጣት በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል።
ባለፉት ዓመታት ካለሙት ሙዝና ማንጎ ልማት ብቻ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ150 ሺህ ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘታቸውንም ገልጸዋል።
"በተለይም በክላስተር በመደራጀታችን የውኃ አጠቃቀማችንና የግብዓት አቅርቦታችንን ለማስተካከል አስችሎናል" ያሉት አርሶ አደሩ፣ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በስፋት የፍራፍሬ ችግኞችን መትከላቸውን ተናግረዋል።
በወረዳው የመንደር 6 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ፀጋነሽ ብዙነህ በበኩላቸው፣ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት በመሳተፋቸው ተጨማሪ ገቢ ማግኘት እንደቻሉ ገልጸዋል።
እስካሁን ሁለት ሄክታር የሚጠጋ መሬትን በሙዝ፣ በማንጎና በፓፓያ ማልማታቸውን ጠቁመው፣ ምርቱን ለቤት ውስጥ ፍጆታ ከማዋል ባሻገር የተረፈውን በመሸጥ በዓመት ከ100 ሺህ ብር በላይ ገቢ እንደሚያገኙ አስረድተዋል።
አርሶ አደር ፀጋነሽ አክለውም፣ የአረንጓዴ ልማቱ የመሬቱን ለምነት በመጨመር ከሰብል ልማት በተጨማሪ በፍራፍሬ ልማትም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረጉን ጠቁመው፣ ያገኙትን ውጤት ለማስቀጠል እንደሚተጉም ገልጸዋል።
የምዕራብ ጎንደር ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ እንደገለጹት፣ በዞኑ በ1 ሺህ 113 ሄክታር መሬት ላይ ቡናና የቆላ ፍራፍሬ የማልማት ሥራ እየተካሄደ ይገኛል።
እስካሁን 117 አልሚ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማቱ በኩታ ገጠም እየተካሄደ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ በዚሁ አሠራር ከ40 ሄክታር በላይ መሬት በፓፓያና በሙዝ ለምቷል ብለዋል።
የምዕራብ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ በአሁኑ ወቅት እየታየ ያለውን አዎንታዊ ውጤት ከአረንጓዴ አሻራ ልማቱ ጋር ይበልጥ በማስተሳሰር የማስፋፋት ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጧል።