ቀጥታ፡

የእንሰት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረጉ የምርምር ሥራዎች ይጠናከራሉ

​ወልቂጤ፣ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡-የእንሰት ተክልን ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡ 

እንሰት ለብዙ ኢትዮጵያውያን የዕለት ተዕለት የምግብ ዋስትና መሠረት በመሆኑ በእንሰት ላይ የሚካሄዱ የምርምር ሥራዎች በሽታን በመቋቋም ምርታማነትን የማሳደግ እና ባህላዊ አሰራርን የማዘመን ጠቀሜታው አላቸው።     

በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የግብርና ምርምር ማስተባበሪያ ጽህፈትቤት ሃላፊ መኩሪያ ታደሰ (ዶ/ር) እንዳሉት የእንሰት ልማት ከአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ ጋር በማጣጣም እየተከናወነ ይገኛል። 

ልማቱ የህብረተሰቡን የምግብ ዋስትንና ለማረጋገጥ እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በሚያስችል መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡ የተሻሻሉ የእንሰት ዝርያዎች ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን ገልጸዋል።

በእንሰት ልማት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንና በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። 

በግብርና ሚኒስቴር የሥራ ሥርና እንሰት ልማት ዴስክ ኃላፊ አቶ ጉቱ ሚጀና እንደገለጹት፣ የእንሰት ልማትን ከአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጋር በማጣጣም እየተከናወነ ይገኛል። 


 

​እንሰት ከፍተኛ የምግብ ምርት የሚሰጥ፣ ድርቅን የሚቋቋም እና የአፈር እርጥበትን የመጠበቅ ተፈጥሯዊ ባህሪ ስላለው ለአረንጓዴ ልማት ሥራው ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል።

የእንሰት ተክልን ምርታማነት ለማሳደግ በምርምር የተደገፈ ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም አመልከተዋል።

የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተርና ተመራማሪ አቶ ቤተል ነክር ማዕከሉ በበኩላቸው፣ በሽታን ተቋቁመው የተሻለ ምርት የሚሰጡ አዳዲስ የእንሰት ዝርያዎችን በስፋት አባዝቶ ለአርሶ አደሩ እያሰራጨ መሆኑን ተናግረዋል።


 

እንሰት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ብቻ በመጠቀም እንደሚለማ ገልጸው፣ ከአካባቢው አርሶ አደሮችና ሌሎች የምርምር ተቋማት ጋር በመቀናጀት ውጤታማ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። 

እንሰት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የአየር ንብረትን ለማስጠበቅና የአፈር እርጥበትን ለመጠበቅ ጠቀሜታ እንዳለው የገለጹት ደግሞ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ ናቸው።


 

ከምግብ ፍጆታነት ባለፈ የአርሶ አደሩ የገቢ ምንጭ እንዲሆንና ከተረፈ ምርቱም የተሻለ ጥቅም ለማግኘት የተሰሩ ሥራዎች ውጤት እያመጡ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

በጉራጌ ዞን የእዣ ወረዳ አርሶ አደር ጀማል ሁሴን  እና ወይዘሮ ነፃነት አርጋ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የእንሰት ችግኞች በማግኘታቸው የተዳከመውን የእንሰት ልማት ሥራቸውን ለማጠናከር መቻላቸውን ገልጸዋል።

ከዚህ በፊት ለእንሰት ተክል ብዙም ትኩረት እንደማይሰጡ አስታውሰው፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተሻሻሉ የእንሰት ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማ መሆን መቻላቸውን ተናግረዋል፡፡ 

የእንሰት ምርታማነትንና ተደራሽነትን ለማሳደግ በሚከናወኑ ተግባራት ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውንም አመልክተዋል። 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም