ኢትዮጵያ ከአህጉራዊ የልማት ዕቅዶች ጋር የተጣጣመ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት አቅም እየገነባች ነው - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ ከአህጉራዊ የልማት ዕቅዶች ጋር የተጣጣመ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት አቅም እየገነባች ነው
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከአህጉራዊ የልማት ዕቅዶች ጋር የተጣጣመ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት አቅም እየገነባች መሆኗን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ።
የምሥራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) አባል ሀገራት የግብርና ትራንስፎርሜሽን አፈጻጸም ግምገማ እና ከ2026 እስከ 2035 የሚተገበረውን የካምፓላ ድንጋጌ ማዕቀፍ አስመልክቶ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የሁለት ቀናት መድረክ ተጠናቋል።
የግብርና ሚኒስትር አማካሪ ዜና ሀብተወልድ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል።
ሀገሪቱ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ በሌማት ትሩፋት፣ በመስኖ ስንዴ እና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ላይ ትኩረት በመስጠት ስኬታማ መሆኗን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ደረጃ በአጀንዳ 2063 የተቀመጠውን የበለጸገች አፍሪካን የመፍጠር ርዕይ ለማሳካት የሚያስችሉ ሥራዎችን በቁርጠኝነት እያከናወነች ትገኛለች ብለዋል።
በመሆኑም አህጉራዊ አቅጣጫዎችን ከሀገራዊ እቅዶች ጋር በማጣጣም የግብርናውን ዘርፍ ይበልጥ ለማሳደግ እና የላቀ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል።
ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እና ምርታማነትን ለማሳደግ በሌማት ትሩፋት፣ በበጋ መስኖ ስንዴና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ላይ ትኩረት በመስጠት ስኬታማ ተግባራትን ማከናወኗን አስረድተዋል።
በምሥራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) የፖሊሲና የምግብ ዋስትና ኤክስፐርት ሲልቪያ ሄንጋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶ አደሩ ማዳረስና አቅሙን መገንባት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
ሀገራዊ እና ቀጣናዊ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እሴት መጨመር፣ በድህረ-ምርት አስተዳደር እንዲሁም አህጉር አቀፍ የንግድ ትስስርን ማጠናከር ላይ ልዩ ትኩረት ሊደረግ እንደሚገባ ገልጸዋል።
በተጨማሪም ሕፃናት እና እናቶች የተመጣጠነ ምግብና አስፈላጊ ንጥረ ነገሮችን እንዲያገኙ መሥራት ወሳኝ መሆኑን አንስተው፣ አባል ሀገራት የግብርና ሥርዓቱን ለማሻሻል በቁርጠኝነት ሊሠሩ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።