የሚዛን አማን ከተማ የመልሶ ማልማት ሥራ ከተማዋን ለኑሮ ምቹና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት ነው - ኢዜአ አማርኛ
የሚዛን አማን ከተማ የመልሶ ማልማት ሥራ ከተማዋን ለኑሮ ምቹና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት ነው
ሚዛን አማን፣ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፡-የሚዛን አማን ከተማ የመልሶ ማልማት ሥራ ከተማዋን ለኑሮ ምቹና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ገለጸ።
የከተማዋ ከንቲባ ኢንጂነር ሰሎሞን ሌዊ ለኢዜአ እንደገለጹት ከተማዋን በተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የመሠረተ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ ነው።
ከተማ አስተዳደሩ የከተማዋን የመልሶ ማልማት ፕሮጀክት ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን ጠቁመው የከተማዋን እድገት የሚመጥኑ አገልግሎት ሰጪ ተቋማትና መሰረተ ልማቶች እንዲከናወኑ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
በከተማዋ ለንግድ፣ ለሆቴልና ለቱሪዝም አገልግሎት የተገነቡ ደረጃቸውን የጠበቁ ሕንጻዎች የኢኮኖሚ እንቅስቃሴውን ከፍ እያደረጉ መሆኑን ጠቅሰዋል።
በዘርፉ እየመጣ ያለውን ለውጥ ለማጠናከር የኤሌክትሪክ አገልግሎት የኃይል ማሻሻያ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድና የውሃ አቅርቦት ትኩረት የተሰጣቸው ተግባራት መሆናቸውን አመልክተዋል።
የመልሶ ማልማቱ ተግባር በኅብረተሰቡ ተሳትፎ ውጤታማ መሆኑን ገልጸው ከከተማ ኮሪደር ልማት ጋር ተሳስሮ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል።
የከተማ ልማት ኢንሼቲቮችን በከተማዋ በማስፋፋት ለነዋሪዎች ምቹና ጽዱ እንዲሁም ለኢንቨስትመንት ተመራጭ ከተማ ለማድረግ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።
የሚዛን አማን አውሮፕላን ማረፊያና የደንቢ ኢኮ ሎጅ ፕሮጀክቶች አገልግሎት መጀመር የቱሪዝም እንቅስቃሴውን በማነቃቃት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደጉ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል ።
በመልሶ ማልማት ሥራ ለተለያዩ አገልግሎቶች ሕንጻ ከገነቡ የከተማዋ ባለሀብቶች መካከል አቶ ተረፈ ገርሲ ልማቱ ለከተማዋ ዕድገት ትልቅ ሚና ተጫውቷል ብለዋል።
ከተማዋ በተለይም ካለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ ፈጣን እድገት እያሳች መሆኑን ገልጸዋል ።
መምህር መላኩ ኬቃብ እና አቶ ስንታየሁ ዳሜ የተባሉ የከተማዋ ነዋሪዎች በበኩላቸው ከተማዋ ፈጣን ዕድገት ላይ መሆኗን የሚያረጋግጡ ተግባራት መሬት ላይ በተጨባጭ እየታዩ መሆኑን ተናግረዋል።
የመልሶ ማልማት ሥራው ከተማዋን በማስፋፋቱ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች መከፈታቸውን የጠቀሱት ነዋሪዎቹ ለዘላቂነቱ የድርሻቸውን ሚና ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።