ቀጥታ፡

የሕገ ወጡ ሕወሓት አመራሮች ያላቸው ብቸኛ አማራጭ ጊዜው ሳይረፍድ እጃቸውን ለፌዴራል መንግሥት መስጠት ነው -አረጋዊ በርሔ (ዶ/ር)

አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ) ፦ የሕገ-ወጡ ሕወሓት አመራሮች ያላቸው ብቸኛ አማራጭ ጊዜው ሳይረፍድ እጃቸውን ለፌዴራል መንግሥት መስጠት ነው ሲሉ የቀድሞው ሕወሃት መስራች አረጋዊ በርሔ (ዶ/ር) ገለጹ።

ዶክተር አረጋዊ በርሔ ኢትዮጵያ ያገጠሟትን ፈተናዎች ሁሉ በድል የመወጣት ልምድ ያላት ጠንካራ ሀገር መሆኗን ለኢዜአ ተናግረዋል።

ከዚህ አኳያ ሕገ-ወጡ ሕወሓት በተለያዩ ጊዜያት በውጭ ኃይሎች ተላላኪነት ኢትዮጵያን ለማተራመስ ያደረጋቸው ሙከራዎችም ሙሉ በሙሉ አልተሳኩም ነው ያሉት።

አሁንም ቢሆን የዚሁ የጥፋት አካል በመሆን የሚያደርገው ጥረት ፈጽሞ የማይሳካና የትም የማያደርሰው መሆኑን አስረድተዋል።

ሻዕቢያ የሚገፋው ያጣ የደረቀ እንጨት ማለት ነው ያሉት ዶክተር አረጋዊ የኤርትራን ወጣት ጨርሶ የትግራይን ወጣት ለእኩይ ዓላማው መጠቀሚያ ለማድረግ እየጣረ ነው ሲሉም አስረድተዋል።

ሕገ-ወጡ ህወሃት ከዚህ ከደረቀ ቡድን ጋር ተጣብቆ የሚያደርገው መፍጨርጨርም መጨረሻው መጥፋት ብቻ መሆኑንም አብራርተዋል።

ስለሆነም የሕገ-ወጡ ቡድን አመራሮች ያላቸው ብቸኛ አማራጭ ከዚህ ቀደም ሲከተሉት የነበረውን አጥፊ አካሄድ በመተው እጃቸውን ለፌደራል መንግሥት መስጠት እንደሆነም መክረዋል።

የፌዴራል መንግሥት በተደጋጋሚ እጁን ለሰላም ሲዘረጋ መቆየቱንና በርካታ ታጣቂዎችም ይህንን ጥሪ በመቀበል ወደ ሰላማዊ ሕይወት በመመለስ ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል።

እንደ ሌሎች ታጣቂዎች ሁሉ የሕገ-ወጡ ሕወሓት አመራሮችም የቀረበላቸውን የሰላም ዕድል እንዲጠቀሙበት ነው አጽኖት ሰጥተው የተናገሩት።

የፌዴራል መንግስት የቡድኑ አመራሮች የሰላም አማራጭን ሲከተሉ እንደሌሎች ታጣቂዎች እንዲቀበላቸው የሚጠበቅብንን ሚና እንወጣለንም ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም