ቀጥታ፡

ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ከማዕድን ተገቢው ገቢ እንዲገኝ በትምህርት፣ በምርምር እና በአቅም ግንባታ ዘርፍ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው

አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከማዕድን ተገቢውን ገቢ እንድታገኝ ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በትምህርት፣ በምርምር እና በአቅም ግንባታ ዘርፍ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አስታወቀ፡፡

የማዕድን ዘርፍ ለአጠቃላይ የኢኮኖሚ ዕድገት እና ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ተለይቶ ትኩረት የተሰጠበት ሲሆን ዘርፉን ለማዘመንና አቅሙን ለማሳደግ በቴክኖሎጂ፣ በጥናትና ምርምር እንዲሁም በባለሙያ ስልጠና ላይ በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።

በተጨማሪም የአካባቢውን ማህበረሰብ ከባህላዊ ወደ ዘመናዊ አሰራር በማሸጋገር፣ ዘላቂና ጤናማ የማዕድን ማውጣት ሂደትን ለመገንባት ጥረት እየተደረገ ነው።

ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በማዕድን፣ በሀገር በቀል እውቀቶች፣ በግብርናና እንስሳት ሀብት እንዲሁም በጤና ዘርፎች ላይ አተኩሮ እየሰራ ይገኛል፡፡

በዩኒቨርሲቲው የስነ-ምድር እና ማዕድን ትምህርት ክፍል ኃላፊ አቶ ሙስጠፋ መሐመድ እንደገለጹት፣ ዩኒቨርሲቲው በአሁኑ ወቅት በዲግሪ እና በማስተርስ ደረጃ በማይኒንግ እና በጂኦሎጂ ትምህርት ተማሪዎችን እያስተማረ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ከማስተማር ስራ ባሻገርም በጥናትና ምርምር የማህበረሰቡን ችግር ለመፍታት በማዕድን ዘርፍ ላይ የተለያዩ ጥናቶችን እያካሄደ መሆኑን አስረድተዋል።

ዩኒቨርሲቲው በሚገኝበት አካባቢ መልካምድራዊ አቀማመጥ በማዕድን የበለጸገ በመሆኑ፣ ይህም ዩኒቨርሲቲው በዘርፉ ላይ ልዩ ትኩረት እንዲያደርግ ካደረጉት ምክንያቶች አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል።

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ለመዓድን ዘርፍ ልዩ ትኩረት መስጠቷን ጠቅሰው፣ ከዘርፉ ማግኘት የሚገባትን ገቢ እንድታገኝ በትምህርት፣ በምርምር እና በአቅም ግንባታ ድጋፍ ዘርፍ የበኩሉን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል፡፡

ከዚህ ቀደም ዘመናዊ ባልሆነ መልኩ ሲካሄድ የነበረውን የማዕድን ስራ ለማዘመን፣ ስልጠናና የአቅም ግንባታ ድጋፍ በመስጠት ማህበረሰቡ ከባህላዊ ወደ ዘመናዊ አሰራር እንዲሸጋገር የሚያስችሉ ስልጠናዎችን እየሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።


 

የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት ገበየሁ አሻግሬ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፣ ዩኒቨርሲቲው ለማዕድን ዘርፍ ልዩ ትኩረት በመስጠት ተገቢ ፕሮግራሞችን ቀርፆ እየሰራ ይገኛል።

ማዕድን በኢንስቲትዩት ደረጃ ራሱን ችሎ እንዲደራጅ ላቦራቶሪዎችን የማደራጀት፣ ልምድ ያላቸውን መምህራን የማሰባሰብ እና ከተለያዩ ትላልቅ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በጋራ በመስራት መማር ማስተማር፣ ምርምር እና የማህበረሰብ አገልግሎት በትብብር እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።

ለዚህም ዘመናዊ ላቦራቶሪ መደራጀቱን ጠቁመው፣ ሀገር ከአካባቢው ልታገኝ የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ በመማር ማስተማር እና በምርምር ስራ ላይ በጋራ እየሰሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።


 

የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ተመስገን ደበሎ (ዶ/ር) በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው ማዕድንን እንደ አንድ ትኩረት አቅጣጫ አድርጎ እንዲሰራበት መንግስት የፈለገበት ዋነኛ ምክንያት የጉጂ አካባቢ በርካታ ማዕድናት የሚገኙበት በመሆኑ ነው ብለዋል።

ለዚህም ነው ዩኒቨርሲቲው ማዕድንን እንደ ዋና የትኩረት አቅጣጫ አድርጎ የሚሰራው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም