በአፍሪካ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለዘር ባንኮች መጠናከርና ለማዳበሪያ ምርት ትኩረት መስጠት ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
በአፍሪካ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለዘር ባንኮች መጠናከርና ለማዳበሪያ ምርት ትኩረት መስጠት ይገባል
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦በአፍሪካ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለሀገር በቀል ዝርያዎች ጥበቃ የሚሆኑ የዘር ባንኮች መጠናከርና ለማዳበሪያ ምርት ዕድገት በትኩረት መስራት እንደሚገባ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ጥበቃ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ ገለፁ።
የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) አባል ሀገራት የግብርና ትራንስፎርሜሽን አፈፃፀም ግምገማ እና ከ2026 እስከ 2035 በሚተገበረው የካምፓላ ድንጋጌ ማዕቀፍን አስመልክቶ በአዲስ አበባ ምክክር መካሄድ ጀምሯል።
ከዛሬ ነሃሴ 11ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ቀናት በሚቆየው የምክክር መድረክ አምስተኛው አጠቃላይ የአፍሪካ የግብርና ልማት መርሐ-ግብር (CAADP) የሁለት ዓመት አፈፃፀም ሪፖርትንና የኢጋድን ቀጣናዊ አፈፃፀም ይገመግማል።
በመድረኩ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ጥበቃ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ አፍሪካ 60 በመቶ ያልታረሰ ለም መሬት እያላት በየዓመቱ ከ100 ቢሊዮን ዶላር በላይ የምግብ ምርትን ከውጭ ለማስገባት ታወጣለች ብለዋል።
የማላቦ የሁለት ዓመት ግምገማ ዘመን ማብቃቱን አንስተው፣ የቀጣይ ትኩረት ውጤታም ትግበራ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል።
አፍሪካ በካምፓላ አጀንዳ አማካኝነት እስከ 2035 የግብርና ምርትን በ45 በመቶ፣ በአህጉር ውስጥ የሚደረግ ንግድን በሶስት እጥፍ ማሳደግ፣ ከምርት ስብሰባ በኋላ የሚባክነውን ምርት በ50 በመቶ መቀነስ እና 100 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት የማሰባሰብ ግብ መቀመጡን ገልጸዋል።
እነዚህን ግቦች ለማሳካት የአፈር ጤናማነት፣ የሀገር በቀል ዝርያዎችን የሚጠብቁ የዘር ባንኮችን ማጠናከር እና አፍሪካ ያላትን የፎስፌትና ፖታሽ ሃብት በመጠቀም ማዳበሪያን በራሷ የማምረት ስራ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ ተናግረዋል።
የካምፓላ አጀንዳ ስኬት የሚለካው በአህጉሪቱ ዜጎች ህይወት ላይ በሚያመጣው ለውጥ መሆኑንም አስገንዝበዋል።
የምስራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የግብርና እና አካባቢ ጥበቃ ዲቪዥን ዳይሬክተርን በመወከል ንግግር ያደረጉት ሲልቪያ ሄንጋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ግጭት፣ የካርቦን ልቀት፣ የአየር ንብረት ለውጥና መፈናቀል የግብርናውን ዘርፍ እየጎዳ መሆኑን አንስተዋል።
በቀጣናው የመስኖ አጠቃቀም ከ20 በመቶ በታች መሆኑንና ኢጋድ የአፈር መረጃ ስርዓትና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓቶችን እየተገበረ መሆኑን አስታውቀዋል።
የግብርና ሚኒስትር አማካሪና የመርሃግብሩ የኢትዮጵያ ተወካይ ዜና ሀብተወልድ ኢትዮጵያ የካምፓላ አጀንዳን ወደ ሀገር በቀል አሰራር ለመቀየር ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር እየሰራች መሆኑን አብራርተዋል።
በአሁኑ ወቅት ሀገሪቱ የሌማት ትሩፋትን ጨምሮ ለዘርፉ የጎላ አስተዋፅኦ ያላቸው መርሃ ግብሮችን በመተግበር ላይ እንደምትገኝም ገልጸዋል።