የአዲስ አበባን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የፍሳሽ ማጣሪያ አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ ሥራ እየተሠራ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ - ኢዜአ አማርኛ
የአዲስ አበባን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የፍሳሽ ማጣሪያ አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ ሥራ እየተሠራ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የፍሳሽ ማጣሪያ አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ ሥራ እየተሠራ መሆኑን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአራብሳ አካባቢ የተገነባውን የንጹህ መጠጥ ውሃ መሠረተ ልማትና የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።
ከንቲባዋ በዚሁ ወቅት፣ ፕሮጀክቱ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትን በጉልህ እንደሚያሳድግ ገልጸዋል።
ባለፉት ዓመታት የንጹህ የመጠጥ ውሃ እጥረትን ለመፍታት የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ የመዲናዋ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በቀን ከ910 ሺህ ሜትር ኪዩብ በላይ መድረሱን አስታውቀዋል።
በቀጣይም ከፍተኛ የማምረት አቅም ያላቸው የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ እንደሚገቡ ተናግረዋል።
በሌላ በኩል የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ የሕብረተሰቡን ጤናና የአካባቢ ጥበቃን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ከንቲባዋ ገልጸዋል።
ጣቢያው ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም መሆኑን በማንሳት፣ መሰል የፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያዎችን በስፋት ለመገንባት መታቀዱን አስረድተዋል።
መሠረተ ልማት መገንባት ብቻውን ግብ አይደለም ያሉት ከንቲባ አዳነች፤ የተገነቡትን መሠረተ ልማቶች መጠበቅና መንከባከብ የሁሉም የጋራ ኃላፊነት ሊሆን እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ከተማ ለማድረግ የተጀመሩት የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በማንሳት፣ ለፕሮጀክቶቹ እውን መሆን አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።
የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ዘሪሁን አባተ በበኩላቸው፤ የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ በቀን 20 ሺህ ሜትር ኪዩብ የማጣራት አቅም እንዳለው ገልጸዋል።
ጣቢያው የከተማዋን የፍሳሽ ማጣራት አቅም በከፍተኛ ሁኔታ የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል።
የከተማዋን እድገት የሚመጥኑ የመጠጥ ውሃና የፍሳሽ ማጣሪያዎች በተለያዩ አካባቢዎች እየተገነቡ መሆናቸውን አንስተዋል።
የዛሬው ቀን የፕሮጀክት መጠናቀቅን ብቻ የሚያሳይ አይደለም ያሉት ደግሞ በአለም ባንክ ምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሪጅን፣ የኢትዮጵያ፣የሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን እና ኤርትራ ተወካይ ዲቪዥን ዳይሬክተር ራጁል አዋስቲ ናቸው።
የኮዬ የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ጣቢያ አዲስ አበባ ንፁህ፣ ጤናማ እና የተሻለች ከተማ ለመሆን የምታደርገው ጉዞ ታሪካዊ ምዕራፍ መሆኑን ጠቁመዋል።
የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የከተሞች የውሃ እና ሳኒቴሽን ዘርፍ የሚያደርገው ተሳትፎ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለውን የረጅም ጊዜ እና ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠውን አጋርነት የሚያንጸባርቅ መሆኑን ተናግረዋል።