ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት በታሪክ መነፅር ሲቃኝ ግልጽና የማያሻማ ነው

አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 9/2018 (ኢዜአ) ፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት በታሪክ መነፅር ሲቃኝ ግልጽና የማያሻማ ነው ሲሉ ምሁራን ገለጹ።

ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሀብቶቿንና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋን ለታዳሽ ኃይል ልማት፣ ቀጣናዊ ትብብር፣ ለጋራ እድገትና ልማት በማዋል ግንባር ቀደም ሚና አላት፡፡

ቅድሚያ ለጎረቤት ሀገራት የሚለው የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ የቀጣናውን ሀገራት በመሰረተ ልማት በማስተሳሰር የጋራ ሰላምና ብልጽግና ማረጋገጥ የሚያስችልም ነው፡፡

የታሪክ ተመራማሪው ፕሮፌሰር አህመድ ዘካሪያ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት የኢትዮጵያ የቀይ ባህር ባለቤትነት በታሪክ መነፅር ሲቃኝ ግልጽና የማያሻማ ነው።

የሀብት ስርጭትንና የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምን በተመለከተም ኢትዮጵያ ከአፍሪካውያን ጋር በጋራ በመጠቀም አህጉራዊ ትብብርን የማጠናከር ፍላጎት አላት ብለዋል።

አፍሪካውያን የተፈጥሮ ሀብቶቻቸውን በጋራና በወንድማማችነት ስሜት መጠቀም አለባቸው ያሉት ፕሮፌሰር አህመድ፤ ኢትዮጵያ ቀጣናውን በውሃና ሀይል ማስተሳሰሯንም ገልጸዋል፡፡

ኢትዮጵያ የቀጣናው ልማትና ደህንነት መልህቅ መሆኗን በመግለጽ፤ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ስራዎችን በመስራትም ግንባር ቀደም መሆኗን ተናግረዋል፡፡

ኢትዮጵያ ከባህር በር የተገለለችው የቀድሞው ህወሓትና ሻዕቢያ የግል ጥቅማቸውን ለማስከበር ሲሉ በፈጠሩት አግላይ አካሄድ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ጥቅሟን የሚያስከብሩ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች እያደረገች መሆኑን ገልጸው፤ ቀጣናዊ የዲፕሎማሲ መድረኮችም ጨምረዋል ብለዋል፡፡

በዚህም ኢትዮጵያ የባህር በር ያስፈልጋታል የሚለው መሠረታዊ እውነትና ፍላጎት በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ አወንታዊ ምላሽ እያገኘ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የቀጣናው ሀገራት በመተጋገዝና በመተባበር አቅማቸውን ማጎልበትና የጋራ ልማትና ዕድገትን ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል፡፡

በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የዲጂታል ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ስለአባት ማናየ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ቀጣናዊና አህጉራዊ ትብብርን ማጠናከር መርሁ ያደረገ ነው፡፡

ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መሥራችና መቀመጫ፣ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት መገኛ እና ለባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ ትኩረት የምትሰጥ ሀገር መሆኗንም ገልጸዋል።

ዓባይን ጨምሮ ወንዞቿን የቀጣናዊ ትስስር፣ የጋራ ዕድገትና የትብብር ማሳያ አድርጋ እንደምትመለከት ገልጸው፤ በዚህም የቀጣናው የታዳሽ ኃይልና የጋራ የልማት መሪነቷን አስጠብቃለች ብለዋል፡፡

የአፍሪካ ሕብረት "አጀንዳ 2063" ለቀጣናዊ የኢኮኖሚያዊ ውህደት ትኩረት እንደሚሰጥ በማንሳት፤ ኢትዮጵያ የሕብረቱን ራዕይ በፅናት ተቀብላ ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በዓባይ ፖለቲከኞች ሴራና በራሳችን ድክመት ለዘመናት ስትጠቀምበት የቆየችውን ቀይ ባህር ማጣቷን አንስተዋል አቶ ስለአባት፡፡

ይሄንን ታሪካዊ ስህተት በማረም ህጋዊ መብቷን ለማስከበር ቀይ ባህርን ወደ ቤቱ የመመለስ እንቅስቃሴ ተጀምሯል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ የህልውና ጉዳይ የሆነው የቀይ ባህር ጥያቄ ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ አንድምታው ከፍተኛ መሆኑን በማንሳት፤ በቀጣናው ያላትን ስትራቴጂያዊ አቅም የሚበይን መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ ጆሮ ገብ እየሆነ መምጣቱን ገልጸው፤ ለቀጣናው ኢኮኖሚያዊ ትብብርና ሰላም የጎላ አበርክቶ ይኖረዋል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም