በክልሉ ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ወደ ሥራ ገብተዋል - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ወደ ሥራ ገብተዋል
ሚዛን አማን፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በ2018 በጀት ዓመት ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ፈቃድ ወስደው ወደ ሥራ መግባታቸውን የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ።
የቢሮው ምክትልና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ከበደ ተስፋዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ክልሉ ለኢንቨስትመንት ሥራ ያለውን አቅም በሚገባ ለመጠቀም በተሰጠው ትኩረት ውጤት እየተገኘ ነው።
በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች በግብርና፣ በአገልግሎት እና በኢንዱስትሪ ዘርፍ ለመሰማራት ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት ፈቃድ መሰጠቱን ተናግረዋል።
ፈቃድ ከተሰጣቸው 123 ባለሀብቶች መካከል 63ቱ በግብርና ዘርፍ መዋለንዋያቸውን ለማፍሰስ ፈቃድ የወሰዱ ሲሆን ይህም የክልሉን ጸጋ መሠረት ያደረገ መሆኑን አመልክተዋል።
በአገልግሎት ዘርፍ በከተሞች የተሻለ ለውጥ እየተመዘገበ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ከበደ፣ በኢንዱስትሪ ዘርፍ ያለውን ውስንነት ለመሙላት የሚያስችል የተቀናጀ እንቅስቃሴ መጀመሩን ጠቁመዋል።
በበጀት ዓመቱ ወደሥራ ለገቡ ባለሀብቶች ከ16 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት እንደተላለፈና ከ110 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩንም ተናግረዋል።
ለባለሀብቶቹ የሥራ ፈቃድ ከመስጠት ባሻገር ለልማት ፕሮጀክቶቻቸው ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ የተናገሩት ኃላፊው በትላልቅ የኢንዱስትሪ ዘርፎች ለሚሠማሩ ባለሀብቶች ክልሉ ልዩ ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል።
በክልሉ ሚዛን አማን ከተማ በሆቴልና ቱሪዝም ኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ዋለልኝ ቸርነት በበኩላቸው፤ መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ወደ ተግባር መግባታቸውን ገልጸዋል።
አካባቢው ከፍተኛ የንግድ እና ሌሎች ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ያለበት መሆኑ ለኢንቨስትመንት ሥራ ውጤታማነት የራሱን አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
በከተማ አስተዳደሩ በኩል የተደረገላቸው የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ሥራቸውን በተሻለ ሁኔታ ለማከናወን አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ጠቁመዋል።
መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የሰጠው ትኩረት በየመስኩ ኢኮኖሚው እንዲነቃቃ አድርጓል ያሉት ደግሞ በግንባታ ሥራ የተሰማሩት አቶ አንድነት ሀብተማርያም ናቸው።
በተለይ በከተሞች በአገልግሎት መስጫ ኢንቨስትመንቶች ላይ እየመጣ ያለውን ለውጥ ተከትሎ የመብራት፣ የመንገድ፣ የውሃና ሌሎች መሠረተ ልማቶች አብረው እየተስፋፉ መሆኑን ተናግረዋል።
ይህም ለተሰማሩበት የግንባታ ዘርፍ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ባሻገር ለከተሞች መስፋፋትና ለአካባቢው ዕድገት በጎ አሻራ ያሳርፋል ብለዋል፡፡