በጉራጌ ዞን የሌማት ትሩፋት መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን እያሳደገ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በጉራጌ ዞን የሌማት ትሩፋት መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን እያሳደገ ነው
ወልቂጤ፣ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ) ፡-በጉራጌ ዞን የሌማት ትሩፋት መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ መምጣቱን በዘርፉ የተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ።
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ በርካታ ዜጎች በዶሮ፣ በወተት፣ በከብት እርባታ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተው ምርታማነታቸውን እያሳደጉ ነው።
መርሃ-ግብሩ በቤተሰብ ደረጃ የምግብና ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርትንና ምርታማነት በማሳደግ ገበያን ለማረጋጋትና ለዜጎች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ለመፍጠር እያስቻለ ነው።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጉራጌ ዞን በሌማት ትሩፋት መርሀግብር ተሰማርተው ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል በዶሮ እርባታ ዘርፍ የተሰማራችው ነፃነት በለጠ፣በአሁኑ ወቅት በእንቁላልና በሥጋ ዶሮዎች እርባታ መሰማራቷን ገልጻ፣ በቀን በአማካይ 200 እንቁላል ለገበያ በማቅረብ በምታገኘው ገቢ የተሻለ ተጠቃሚ መሆኗን ተናግራለች።
ሌላኛው በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት የተሰማሩት አቶ ገብሩ ታፈሰ ጾሙን ሲያድር በነበረ 2 ሄክታር መሬት ላይ ልማታቸውን አጠናክረው በመቀጠል የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርታቸውን ለገበያ ማቅረብ መጀመራቸውን ገልጸዋል።
የረሻድና ቤተሰቦቹ የተቀናጀ እንስሳት ልማት ሥራ አስኪያጅ አብደራዛቅ ከድር እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በፈጠረላቸው ምቹ ዕድል በወተት ልማት፣ በእንስሳት እርባታና በንብ ማነብ ሥራ ተሰማርተው ውጤታማ ሆነዋል።
የተቀናጀ የእንስሳት ልማት ምርታማ እንዳደረጋቸው ጠቅሰው፣ በወተት ልማቱ በቀን በአማካይ 60 ሊትር ወተት እንደሚያገኙ ተናግረዋል።
ከዚህ በተጨማሪ ያረቧቸውን የሥጋ ከብቶች በመሸጥ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ተናግረዋል።
የጉራጌ ዞን አስተዳደር ግብርና መምሪያ በበኩሉ በዞኑ የሌማት ትሩፋት መርሀግብሩን ወጤታማ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ በተከናወኑ ሥራዎች አመርቂ ወጤት መመዝገቡን ተናግረዋል።
የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ እና የግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዞኑ በስፋት እየተተገበረ ይገኛል።
በተለይም በወተትና በእንቁላል ምርትና መርታማነትን በማሳደጉ በአካባቢው የነበረውን የአቅርቦት እጥረት በመፍታት በኩል ጉልህ አስተዋጾ ከማድረግ ባለፈ በዘርፉ የተሰማሩትን የተሻለ ተጠቃሚ አድርጓቸዋል ብለዋል።
መርሀግብሩን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ በአሁኑ ወቅት ዝርያቸው ለተሻሻሉ የወተት ላሞች አቅርቦትና ለዶሮ እርባታ ልማት ልዩ ትኩረት መሰጠቱንም አስታውቀዋል።
ከዚህ በተጨማሪ በሌማት ትሩፋት ለተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ከማገዝ ባለፈ በዘርፉ የሚሰማሩትን የህብረተሰብ ክፍሎች ቁጥር በማሳደግ ለማስፋፋት ይሰራል ብለዋል።