ቀጥታ፡

በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በከተሞቹ የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል

ሆሳዕና ፤ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ) ፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ሆሳዕና፣ በቡታጅራና በወልቂጤ ከተሞች የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች መከናወናቸው ተመላከተ፡፡

የከተሞቹ አስተዳደሮች ከንቲባዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል።

የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሳሙኤል ሽጉጤ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት አገልግሎትን ለማዘመን የሚያስችል መሶብ የአንድ ማዕከል፣ የጤና ተቋማት፣ የውስጥ ለውስጥ አስፋልት መንገድ እና የ12 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል ብለዋል፡፡

ይህም ከተማዋን ጽዱ፣ ውብና ለነዋሪው ምቹ፣ ለኢንቨስትመንትና ለኮንፈረንስ ቱሪዝም ተመራጭ እንድትሆን አስችሏል ነው ያሉት።

የከተማው ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ መሰብሰብና የማህበረሰቡን ተሳትፎ ማዕከል ያደረጉ ስራዎችን ተግባራዊ የማድረጉ ሂደት በተያዘው በጀት ዓመትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።


 

የቡታጅራ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አብዱ አህመድ በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ የልማት ስራዎች ተግባራዊ መደረጋቸውን ተናግረዋል።

አስተዳደሩ የማህበረሰቡን ተሳትፎና የውስጥ አቅምን በመጠቀም ተግባራዊ በማድረግ ላይ ከሚገኘው የ25 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ውስጥ 11 ነጥብ 26 ኪሎ ሜትሩ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል ነው ያሉት።

ይህም ከተማዋን ለኑሮ ምቹ፣ ሳቢና ማራኪ ከማድረግ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዋ እንዲነቃቃ ማድረጉን ገልጸዋል።

በከተማው እየተተገበረ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ስራ ወልቂጤን ለነዋሪዎቿ ምቹና ተመራጭ እንድትሆን አድርጓታል ያሉት ደግሞ የከተማዋ ከንቲባ ሙራድ ከድር ናቸው።


 

በልማት ስራውም የማህበረሰቡ ተሳትፎና ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱን እንዲሁም የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ በ2019 ዓ/ም የትኩረት አቅጣጫ ዙሪያ ከክልል፣ ከዞንና ከከተማ አስተዳደር አመራሮች ጋር በቡታጅራ ከተማ የምክክር መድረክ ማካሄዱ ይታወሳል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም