በምስራቅ ሸዋ ዞን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የግብርና ምርቶች ኤክስፖርትን ለማሳደግ የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው ቀጥለዋል - ኢዜአ አማርኛ
በምስራቅ ሸዋ ዞን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የግብርና ምርቶች ኤክስፖርትን ለማሳደግ የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው ቀጥለዋል
አዳማ፤ ነሐሴ 5/2018(ኢዜአ) ፡-በምስራቅ ሸዋ ዞን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የግብርና ምርቶች ኤክስፖርትን ለማሳደግ የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባቡ ዋቆ ገለፁ።
የምስራቅ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባቡ ዋቆን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ የዞኑ አመራሮች በቦሰት ወረዳ በኩታገጠም የለማውን የቦሎቄና በቆሎ ሰብል ያለበትንና የእንክብካቤ ሂደትን ጎብኝተዋል።
አቶ አባቡ ዋቆ በወቅቱ እንዳሉት፤ በዞኑ በምግብ ራስን ለመቻልና የኤክስፖርት ምርቶችን ለማሳደግ የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት እየሰራን ነው።
በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን ከ580 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዋና ዋና ሰብሎች በቴክኖሎጂ በታገዘ አሰራር በዘር መሸፈኑን ለአብነት አንስተዋል።
በተለይም በዘንድሮው ዓመት የአርሶአደሩን ምርትና ምርታማነት ለመጨመር የሜካናይዜሽን አገልግሎቱን በስፋት ለአርሶአደሩ ተደራሽ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል።
አጠቃላይ በሰብል ከተሸፈነው የዞኑ መሬት ውስጥ ከ91 በመቶ በላይ በሜካናይዜሽን በመደገፍና ቴክኖሎጂን በመጠቀም በኩታገጠም የለማ መሆኑንም አንስተዋል።
በዋናነት ከውጭ የሚገቡ የግብርና ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ የኤክስፖርት ምርቶችን ለማሳደግ የተቀመጠውን ሀገራዊ ግብ እውን ለማድረግ በሚደረገው ሂደት ውስጥ የዞኑ ድርሻ የላቀ ነው ብለዋል።
ለዚህም አርሶአደሩ ገበያ ተኮር ምርቶችን በተለይም ቦሎቄ፣ ማሾ፣ ሽንብራ እንዲሁም ስንዴን በስፋት በኩታገጠም እያለማ ይገኛል ብለዋል።
በየደረጃው የሚገኙ የዞኑ አመራሮች በየዕለቱ በአርሶአደሩ ማሳ በመገኘት ቡቃያው የለበትን ሁኔታ በመመልከት በእንክብካቤው በተለይም በአረምና የሰብል በሽታን በመከላከል ላይ የተሟላ እገዛ ማድረግ የጉብኝቱ ዓላማ መሆኑንም ተናግረዋል።
የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ መስፍን ተሾመ በበኩላቸው በዞኑ ከመደበኛው የሰብል ልማት በተጓዳኝ የግብርና ኤክስፖርት ምርቶች ላይ እየሰራን ነው ብለዋል።
በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ88ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቦሎቄ በኩታገጠም መልማቱን ለአብነት አንስተዋል።
ከዚህም ከሁለት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል ያሉት አቶ መስፍን፤ ከሚገኘው ምርትም 900 ሺህ ኩንታል ያህሉ ወደ ውጭ ይላካል ብለዋል።
የኤክስፖርት ቦሎቄ ልማቱን አርሶአደሮቹ ከባለሀብቶች ጋር በኮንትራት እርሻ ውል እያለሙ መሆኑንም ገልጸዋል።