ቀጥታ፡

በሙስናና ሕገ ወጥ ድርጊት የተሰማሩ አካላትን ተጠያቂ የማድረግ ርምጃ ቀጣይነት ሊኖረው ይገባል

አዲስ አበባ፤ነሐሴ 5/2018 (ኢዜአ)፦የመንግሥት በሙስናና ሕገ ወጥ ድርጊት የተሰማሩ አካላትን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ርምጃ ቀጣይነት ሊኖረው እንደሚገባ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡

ህገወጥነትን በመከላከልና በማጋለጥ በኩል ህብረተሰቡ ተሳትፎውን ማጠናከር እንዳለበትም ጠቁመዋል። 

መንግሥት በተደራጀ ሙስናና ሕገወጥ ድርጊቶች የተሰማሩ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር በማዋል የሕግ የበላይነትን እያረጋገጠ እንደሚገኝ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በሰጠው መግለጫ አሳውቋል፡፡

ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ የተቀመጠውን ራዕይ ለማሳካት ከልማት ሥራዎች ባሻገር የሕግ የበላይነትን ማስፈን ቀዳሚ ተግባሩ አድርጎ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡

የመንግሥትን ሕግ የማስከበር ርምጃ በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እንዳሉት፤ የህዝብን ሀብት ከምዝብራና ብክነት መጠበቅ የመንግሥት ትኩረት ሊሆን ይገባል፡፡

በቅርቡ መንግሥት በሙስናና ሕገ ወጥ ድርጊቶች ላይ የተሳተፉ አካላትን በቁጥጥር ስር በማዋል ተጠያቂነትን ለማስፈን የወሰደው እርምጃ ተገቢና ቀጣይነት ሊኖረው የሚገባ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ከአስተያየት ሰጭዎች መካከል ሄኖክ ተስፋዬ፤ ርምጃዎቹ የሕግ የበላይነትን በማስፈን የመንግስትና የህዝብን ሀብት ከምዝበራ ማዳን ነው ብለዋል፡፡

በብልሹ አሰራርና ባልተገቡ አሰራሮች ላይ እየተወሰደ ያለው ርምጃ የመንግሥትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እና በዜጎች ዘንድ ደግሞ መተማመንን የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል፡፡


 

ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ትዕግስት ገብረየስ፤ መንግሥት ተጠያቂነትን ለማስፈን የሚወስደው ርምጃ እስከታች ባለው የመንግሥት መዋቅር ገቢራዊ መደረግ አለበት ብለዋል፡፡

መንግሥት ተጠያቂነትን ለማስፈን የጀመረው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን በማንሳት፤ ሂደቱ ቀጣይነት ሊኖረው እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

ወጣት ቴዲ ዑለማ  በበኩሉ፤ መንግሥት የህግ የበላይነትን ለማስፈን የተግባር ቁርጠኛ መሆኑን ያሳየ ርምጃ መሆኑን ተናግሯል፡፡


 

ሌላው አስተያየት ሰጪ አቢቲ ረጋሳ ሙስናና ብልሹ አሰራር የዕድገት ማነቆ መሆኑን በመግለጽ፤ ርምጃው አስተማሪና ትምህርት ሰጭ ነው ብለዋል፡፡


 

ማንም ሳይለፋና ሳይሰራ መበልጸግ የለበትም፤ ሙሰኞችን ለህግ ማቅረብ ተጠናክሮ መቀጠል ህዝቡም መተባበር አለበት ያሉት ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ በለጡ ዘላለም ናቸው፡፡


 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም